ፈልግ

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ጸሎት፣ ሕይወት፣ እምነት የክርስቲያን ሕይወት ነበልባል እንዲበራ ያደርጋሉ አሉ!

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ዘወትር ረቡዕ እለት ከቫቲካን ሆነው የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ የሚታወቅ ሲሆን በእዚህ መሰረት ቅዱስነታቸው በሰኔ 02/2013 ዓ.ም ያደረጉት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ከእዚህ ቀደም በጸሎት ዙሪያ ላይ ጀመረውት ከነበረው አስተምህሮ ቀጣይ ክፍል እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን ጸሎት ፣ ሕይወት ፣ እምነት የክርስቲያን ሕይወት ነበልባል እንዲበራ ያደርጋሉ ማለታቸው ተገልጿል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ክብራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያደረጉትን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አሰምህሮ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አሰናድተነዋል እንድትከታተሉን ከወዲሁ እንጋብዛለን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

ከዚህ ቀደም በጸሎት ዙሪያ ላይ ጀምረነው የነበረው የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ የመጨረሻ ክፍል ላይ ጽንቶ መጸለይን በተመለከተ በዚህ ዙሪያ ላይ ዛሬ እንነጋገራለን። እሱ ግብዣ ነው ፣ በእርግጥም ከተቀደሰው መጽሐፍ  ቅዱስ ወደ እኛ የሚመጣ ትእዛዝ ነው። የሩሲያ መንፈሳዊ ጉዞ የሚጀመረው ቅዱስ ሐዋርያው ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ሰዎች በጻፈው የመጀሪያ መልእክት ላይ በተጠቀሰው “ሳታቋርጡ ጸልዩ፤ በማናቸውም ሁኔታ አመስግኑ” (1ተሰሎንቄ 5፡17-18) በሚለው ሐረግ ነው። የሐዋርያው ​​ቃላት ሰውዬውን ነኩት እናም ህይወታችን በብዙ የተለያዩ ጊዜያት የተቆራረጠ በመሆኑ ሁል ጊዜም ትኩረትን መስጠት የሚቻል ስለማይሆን ያለማቋረጥ መጸለይ እንዴት ይቻል እንደነበር አስቦ ነበር። ከዚህ ጥያቄ ፍለጋውን ይጀምራል ፣ ይህም የልብ ጸሎት ተብሎ የሚጠራውን እንዲያገኝ ይመራዋል። እሱ ከእምነት ጋር በተጋመደ መልኩ “የእግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ፣ እኔን ኃጢአተኛውን ማረኝ!” የሚለውን በመድገም ያጠቃለላል። ቀስ በቀስ ራሱን ከትንፋሽ ምት ጋር የሚስማማ እና ቀኑን ሙሉ የሚዘልቅ ጸሎት ይሆናል። በእርግጥ እስትንፋሱ በጭራሽ አይቆምም ፣ እኛ በምንተኛበት ጊዜም እንኳ። ጸሎት የሕይወት እስትንፋስ ነው።

እንግዲያውስ ሁል ጊዜ የጸሎት ሁኔታን ጠብቆ ማቆየት የሚቻለው እንዴት ነው? የክቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ የክርስቲያን ሕልውና ሙሉ አካል ሊሆን ስለሚችል ቀጣይነት ያለው ጸሎት አስፈላጊነት ላይ አጥብቆ የሚደግፍ ከመንፈሳዊ ታሪክ ውስጥ የሚመነጭ ውብ ጥቅሶችን ይሰጠናል። እስቲ አንዳንዶቹን እንመልከት።

መነኩሴው ኤቫግሪየስ ፖንቲከስ ይህንን ሲያረጋግጥ “ያለማቋረጥ ለመሥራት፣ ነቅተን ለመጠበቅ እና ለመጾም አልታዘዝንም፣ ነገር ግን ያለማቋረጥ እንድንጸልይ ተደንግጓል” (የክቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ቁ። 2742) ይለናል። ስለዚህ በክርስቲያን ሕይወት ውስጥ በጭራሽ መሳት የማይኖርበት ግትር የሆነ ነገር አለ ማለት ነው። በጥንት ቤተመቅደሶች ውስጥ ተጠብቆ የነበረ ፣ ያለማቋረጥ የሚነድ እና ካህናቱ እንደ በራ እንዲኖር የማድረግ ተልእኮ የነበራቸው ያ ቅዱስ እሳት በውስጣችን ሊነድ ይገባዋል። ስለዚህ ያለማቋረጥ የሚነድ እና ማንም ሊያጠፋው የማይችል ቅዱስ እሳት በውስጣችን ሊኖር ይገባል።

ለእውነተኛ ሕይወት ከፍተኛ ትኩረት ይሰጥ የነበረው የቤተክርስቲያን እረኛ ቅዱስ ዮሐንስ ክርዞስቶም “በሕዝብ መካከል በምትጓዙበት ወይም በመደብራችሁ ውስጥ በመግዛት ወይም በመሸጥ ላይ እያላችሁ፣ ወይም ምግብ በምታበስሉበት ሰዓት እንኳን የጋለ ልባዊ ጸሎት ማቅረብ ትችላላችሁ” (የክቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ቁ. 2743) በማለት ይሰብክ ነበር። ስለዚህ ፀሎት የህይወታችንን ዜማ የምንቀዳበት አንድ ዓይነት የሙዚቃ ቅኝት ነው። ከዕለታዊ ሥራ ጋር ተቃራኒ አይደለም ፣ ከብዙ ትናንሽ ግዴታዎች እና ኃላፊነቶች ጋር አይቃረንም ፣ እንዲያውም እያንዳንዱ ድርጊት ትርጉሙን ፣ ምክንያቱን እና ሰላሙን የሚያገኝበት ቦታ ነው።

በእርግጠኝነት እነዚህን መርሆዎች በተግባር ላይ ማዋል ቀላል አይደለም። በሺዎች ተግባራት የተጠመዱ አባት እና እናት በሕይወታቸው ውስጥ መደበኛ ጊዜዎችን እና ለጸሎት ቦታዎችን ማግኘት ቀላል ስለማይሆን በሕይወታቸው ውስጥ ለተወሰነ ጊዜ የጸሎት ናፍቆት ሊሰማቸው ይችላል። ከዚያ በኋላ ለልጆች ፣ ለሥራ ፣ ለቤተሰብ ሕይወት ፣ የእድሜ ባለጸጋ የሆኑ ቤተሰብ ያላቸው ሰዎች እነርሱን ለመንከባከብ… አንድ ሰው በነዚህ ነገሮች ሁሉ ማለፍ በጭራሽ አይቻልም የሚል አመለካከት ሊኖረው ይችላል። እናም አጽናፈ ሰማይን ሁሉ መንከባከብ ያለበት አባታችን እግዚአብሔር ሁልጊዜ እያንዳንዳችንን እንደሚያስብ ማሰቡ ለእኛ ጥሩ ነው። ስለሆነም እኛም ሁሌም እርሱን ማስታወስ አለብን!

በተጨማሪም በክርስቲያናዊ መነኮሳት ሕይወት ውስጥ ሥራ ሁል ጊዜ ለራሳቸው እና ለሌሎች የማቅረብ ሥነ ምግባራዊ ግዴታ ብቻ ሳይሆን ለአንድ ዓይነት ውስጣዊ ሚዛን እንዲሁ በታላቅ አክብሮት እንደተያዘ ማስታወስ መልካም ነው፣  የሰው ልጅ እንዲህ ዓይነቱን ፍላጎት ማዳበሩ አስፈላጊ ነው፣ ጸሎት ረቂቅ ስለሆነ ከእውነታው ጋር ያለውን ግንኙነት እንዳያጣ መጣር ይኖርብናል። ከእውነታው ጋር እንደተገናኘን እንድንቆይ ሥራ ይረዳናል። የመነኩሴ እጆች በጸሎት የተዋሃዱት አካፋዎችን እና መቆፈሪያ የሚይዙትን ሰዎች ጥሪዎችን ይይዛሉ። በሉቃስ ወንጌል (10: 38-42) ውስጥ ኢየሱስ ለቅድስት ማርታ በእውነት አስፈላጊ የሆነው እግዚአብሔርን ማዳመጥ ብቻ እንደሆነ ነግሮታል ፣ በምንም መንገድ እሷ የነበራትን አገልግሎት ሁሉ ለማቃለል ያለመ አነጋገር ግን አልነበረም። በእንደዚህ ዓይነት ጥረት መከናውን እንደ ሚገባው ነው ያሳየው።

በሰው ልጅ ውስጥ ያለው እያንዳንዱ ነገር “ሁለትዮሽ” ነው- ሰውነታችን የተመጣጠነ ነው ፣ ሁለት እጆች ፣ ሁለት ዓይኖች ፣ ሁለት እግሮች አሉን… እናም ስለዚህ ፣ ሥራ እና ጸሎት እንዲሁ ተጓዳኝ ናቸው። ጸሎት - የሁሉም ነገር “እስትንፋስ” ነው - ይህ ግልጽ ባልሆነባቸው ጊዜያትም ቢሆን እንደ ህያው የሥራ መስክ ሆኖ ይቀራል። በስራ ብዛት የተነሳ ለጸሎት ጊዜ ማጣታችን ሰብዓዊነት የጎደለው ነገር ነው።

በተመሳሳይ ጊዜ ከህይወት የራቀ ጸሎት ጤናማ አይደለም። ከሕይወት ተጨባጭነት የሚለይ ጸሎት መንፈሳዊነት ወይም ሥነ-ሥርዓታዊ ይሆናል። ኢየሱስ በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ለደቀ መዛሙርቱ ክብሩን ካሳየ በኋላ ያንን የደስታ ጊዜ ለማራዘም አልፈለገም ፣ ይልቁንም ከእነሱ ጋር ከተራራው ወርዶ የዕለት ተዕለት ጉዞውን መቀጠሉን እናስታውስ። ምክንያቱም ያ ተሞክሮ እንደ እምነታቸው ብርሃን እና ጥንካሬ በልባቸው ውስጥ መቆየት ነበረበት።በዚህ መንገድ ፣ ከእግዚአብሄር ጋር ለመቆየት የወሰነው ጊዜ በህይወት ተግባራዊነት የሚረዳን እምነትን ያድሳል ፣ እናም እምነት ደግሞ ያለማቋረጥ ፀሎትን ይንከባከባል። በእምነት ፣ በሕይወት እና በጸሎት መካከል ባለው በዚህ ክበብ ውስጥ እግዚአብሔር ከእያንዳንዳችን ያን የክርስቲያን ሕይወት ነበልባል ጠብቀን እንድንቆይ ይፈልጋል።

ይህንን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከእዚህ በታች ያለውን የማጫወቻ ቁልፍ ይጫኑ!
09 June 2021, 11:05

በቅርብ ጊዜ ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር የተደረገው ግንኙነት

ሁሉንም ያንብቡ >