ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በኢራቅ ሞስሎ ከተማ በተገኙበት ወቅት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በኢራቅ ሞስሎ ከተማ በተገኙበት ወቅት  

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ለኢራቅ እና ለመላው ዓለም የወንድማማችነት መንፈስ መፍጠር ተግዳሮት ነው አሉ!

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በመጋብት 01/2013 ዓ.ም ባደረጉት ሳምንታዊው የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ትኩረቱን አድርጎ የነበረው እርሳቸው ከየካቲት 26-29/2013 ዓ.ም ደረስ በኢራቅ አድርገውት በነበረው 33ኛውን ሐዋርያዊ ጉዞ ላይ በተንፀባረቁት አብይት ክንውኖች ላይ ያተኮረ እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን በጉብኝታቸው ወቅት የተሰማቸውን የጸጸት ስሜት እንዲሁም የኢራቅ ህዝብ የክርስቶስን መልእክት በደስታ በመቀበላቸው የተሰማቸውን ደስታ አጉልተው ገልጸዋል።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያደረጉትንን ንግግር ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አሰናድተነዋል ተከታተሉን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

ባለፉት ጥቂት ቀናት ውስጥ ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ በጊዜያቸው ወደ ኢራቅ ለማድረግ አቅደውት የነበረውን ሐዋርያዊ ጉብኝት እውን ለማድረግ ጌታ ኢራቅን እንድጎበኝ ፈቅዶልኝ ነበር። ከእዚህ ቀደም አንድ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት የአብርሃም ምድር ረግጦ አያውቅም ነበር። ከዓመታት ጦርነት እና ሽብርተኝነት አደጋ በኋላ እየተከሰተ በሚገኘው ከባድ ወረርሽኝ ወቅት ይህ የተስፋ ምልክት ሆኖ አሁን እንዲከሰት የመለኮታዊ ፈቃድ ሆነ።

ከዚህ ጉብኝት በኋላ ነፍሴ በምስጋና ተሞልታለች - ለእግዚአብሄር እና ይህ ጉብኝት እውን እንዲሆን ላስቻሉት ሁሉ አመስጋዬን እያቀረብኩኝ፣ ለሪፐብሊኩ ፕሬዝዳንት እና ለኢራቅ መንግስት ፣ ለሀገሪቱ ፓትርያርኮች እና ጳጳሳት ፣ ለሁሉም አገልጋዮች እና ለሚመለከታቸው አብያተ ክርስቲያናት ምእመናን አባላት ፣ ለታላላቆቹ ባለሥልጣናት ፣ ለታላቁ አያቶላ አል-ሲስታኒ ጨምሮ እያመሰገንኩኝ በነጃፍ በሚገኘው መኖሪያው ውስጥ የማይረሳ ስብሰባ አደረጌ ነበር።

ይህ ሐዋርያዊ ጉብኝት የንስሐ ስሜት እንዲሰማኝ አድርጓል - ለዓመታት የተጫነባቸው መስቀል በካቶሊክ ቤተክርስቲያን ስም ወደ እዚያ አገር ሰዎች ራሴን ቅርብ ባለማድረጌ፣ ወደዚያ ሰማዕት ቤተክርስቲያን መቅረብ ባለመቻሌ፣ በቃራቆሽ መግቢያ ላይ ወደ ተቀመጠው ግዙፍ መስቀል ራሴን ቅርብ ባለማድረጌ አዝናለሁ። በተለይ ቁስሎቹ አሁንም ክፍት ሆኖ እንዳሉ መመልከቴ እጅግ በጣም ተሰምቶኛል፣ የበለጠ ደግሞ ከዓመፅ እና ከስደት የተረፉትን ሰዎች ተገናኝቼ ምስክርነታቸውን ስሰማ እጅግ በጣም አዝኜ የነበረ ሲሆን እናም በተመሳሳይ ጊዜ የክርስቶስን መልእክት በመቀበል ደስታን በዙሪያዬ አየሁ። ለእዚህ ሐዋርያዊ መልእክት የተመረጠው መሪ ቃል በሆኑት በኢየሱስ ቃላት ውስጥ “ሁላችሁም ወንድማማቾች ናችሁ” (ማቴ 23፡8) የሚለው ሲሆን አጠቃላይ ለሰላም እና ለወንድማማችነት አድማስ የመክፈት ተስፋን ስንቄ ወደ እዚያው አቅንቼ ነበር፣ ያንን ተስፋ በእዚያ አገር ውስጥ ተመልክቻለሁ። በሪፐብሊኩ ፕሬዝዳንት ንግግር ውስጥ ይህ ተስፋ ተሰማኝ። በብዙ ሰላምታዎች እና ምስክርነቶች፣ ሕዝቡ ባቀረበው ሙዚቃዎች እና ያሳያቸው ምልክቶች ውስጥ ተገነዘብኩ። በወጣቶች ብሩህ ገፅታዎች ላይ እና በአረጋውያን ንቁ በሆኑ ዓይኖች ላይ ይህንን ተስፋ አነበብኩኝ።

የኢራቅ ህዝብ በሰላም የመኖር መብት አለው ፤ የእነሱ የሆነውን ክብራቸውን እንደገና የማግኘት መብት አላቸው። የእነሱ ሃይማኖታዊ እና ባህላዊ መሰረታቸው ከሺዎች ዓመታት በፊት የተጀመሩ ናቸው-የሜሶፖታሚያ የሥልጣኔ መነሻ ናት። በታሪክ ደረጃ ባግዳድ በመጀመሪያ ደረጃ አስፈላጊነት ከተማ ናት። ለብዙ መቶ ዘመናት በዓለም ውስጥ እጅግ ብዙ መጽሐፍት ያለው ቤተ-መጻሕፍት ነበራት። እና ማን አጠፋው? ጦርነት። ጦርነት ሁል ጊዜ በዘመን ለውጥ ራሱን የሚቀይር እና የሰውን ልጅ መብላት የሚቀጥል ጭራቅ ነው፣ ጦርነት። ነገር ግን ለጦርነት የሚሰጠው ምላሽ ሌላ ጦርነት አይደለም ፣ ለመሣሪያዎች የሚሰጠው ምላሽ ሌሎች መሳሪያዎች አይደሉም። ምላሹ ወንድማማችነት ነው። ይህ ለኢራቅ ብቻ ሳይሆን ለሁላችንም ተግዳሮት ነው። በግጭቶች ውስጥ ለብዙ ክልሎች እና በመጨረሻም ለመላው ዓለም ተግዳሮት የሚሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ።

በዚህ ምክንያት እኛ ከአራት ሺህ ዓመታት በፊት አብርሃም የእግዚአብሔርን ጥሪ በተቀበለበት በዑር አገር ከሚገኙ የክርስቲያን እምነት ተወካዮች እና ከሙስሊም እምነት ተከታዮች እንዲሁም ከሌሎች የሐይማኖት ተቋማት ተወካዮች ጋር ተገናኝተን በጋራ ጸሎት አቅርበን ነበር። አብርሃም ብዙ ዘር እንደ ሚሰጠው ቃል የገባለትን የእግዚአብሔርን ቃል ስለሰማ በእምነት አባታችን ነው። ሁሉንም ነገር ትቶ ሄደ። እግዚአብሔር ለተስፋዎቹ ታማኝ ነው እናም እስከ ዛሬ ድረስ ወደ ሰላም የሚወስደውን እርምጃችንን ይመራል። ወደ ሰማይ እይታቸውን በማደረግ በምድር ላይ የሚጓዙትን ሰዎች እርምጃዎች ይመራል። እናም በኡር - በእነዚያ ብሩህ ሰማይ ስር አብረን ቆመን ፣ በሰማይ የሚገኘው አባታችን አብርሃም ያየነው ተመሳሳይ ሰማይ እየተመለከትን፣ እኛ የእርሱ ዘር ማምዘር የሆንን - ሁላችሁም ወንድማማቾች እና እህተማማቾች ናችሁ የሚለውን በጋራ የምናስተጋባ ይመስላል።

በባግዳድ ሲሪያክ-ካቶሊክ ካቴድራል ቤተክርስትያን ውስጥ በነበረን ግንኙነት የወንድማማችነት መልእክት የተገኘ ሲሆን በመስዋዕተ ቅዳሴ ስነ ስርዓት ወቅት ከመካከላቸው ሁለቱ ካህናት የሚገኙበት አርባ ስምንት ሰዎች የተገደሉ ሲሆን በኢራቅ ያለው ቤተክርስቲያን የሰማዕት ቤተክርስቲያን ናት። እናም በእነዚያ ሰማዕታት መታሰቢያ በድንጋይ ላይ ፅሁፍ በተጻፈበት በዚያ ቤተክርስቲያን ውስጥ መገኜቴ ደስታን ፈጠረበኝ። በመካከላቸው መሆኔ ያስገረመኝ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት በመካከላቸው መገኘታቸው ከሚያስገኘው ደስታ ጋር ተቀላቀለብኝ።

በጥንታዊቷ የነነዌ ከተማ ፍርስራሾች አጠገብ ከሞሱል እና ከትግሪስ ወንዝ አጠገብ ከቃራቆሽ ከተማን ጨምሮ የወንድማማችነት መልእክት ማስተላለፍ ጀምረን ነበር። የአይ ሲስ የአሸባሪዎች ቡድን በወረራው በሺዎች እና በሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች አገራቸውን ጥለው እንዲሸሹ እና አገራቸውን ለቀው እንዲወጡ ምክንያት ሆኗል፣ ከእነዚህም መካከል ብዙ ክርስቲያኖች እና እንዲሁም የተለያዩ እምነቶችን የሚከተሉ ሰዎች፣ በቁጥር አናሳ የሆኑ በተለይም ያዚዲ ጎሳዎች ይገኙበታል። የእነዚህ ከተሞች ጥንታዊ ማንነት ወድሟል። አሁን እንደገና ለመገንባት ከፍተኛ ጥረት እያደረጉ ነው። ሙስሊሞቹ ክርስቲያኖች ከተሰደዱበት ስፍራ ተመልሰው እንዲመጡ እና እንዲመለሱ ክርስቲያኖቹን እየጋበዙ ሲሆን አብረዋቸው አብያተ ክርስቲያናትን እና መስጊዶችን እያደሱ ይገኛሉ። እናም እባካችሁ ለእነዚህ በጣም ለተጎዱ ወንድሞቻች እና እህቶቻች መጸለያችንን እንቀጥል ፣ እናም እንደገና ለመጀመር ጥንካሬ እንዲኖራቸው በተቻለን አቅም የበኩላችንን እናድርግ። ስለ ተሰደዱት ብዙ ኢራቃውያን ሳስብ ለእነሱ ልነግራቸው የምፈለገው ነገር ቢኖር -እንደ አብርሃም ሁሉንም ነገር ትታችሁ ሂዳችኋል፣ እንደ እርሱ እምነት እና ተስፋችሁን ጠብቃችሁ ኑሩ ለማለት እፈልጋለሁ። የትም ብትሆኑ የወዳጅነት እና የወንድማማችነት ሽመና መሸመናችሁን አታቁሙ።

የወንድማማችነት መልእክት በተደርጉት ሁለት መስዋዕተ ቅዳሴዎች ውስጥ የተላለፈ መልእክት ነው፣ አንዱ በባግዳድ በካልዳዊያን የስርዓተ አምልኮ ደንብ መሰረት የተደረገ ሲሆን ሌላው ደግሞ  በክልሉ ፕሬዝዳንት እና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ፣ በባለስልጣናት እና በሕዝብ ዘንድ አቀባበል በተደረገልኝ ከተማ በሆነችው በኤርቢል መልእክቴን አስተላልፊያለሁኝ። የአብርሃም ተስፋ እና የእርሱ ዘሮች የሆንን የእኛም ተስፋ ባከበርነው ሚስጥር ውስጥ እግዚአብሔር አብ ለእኛ ሲል ለሁሉም ሰው መዳን አሳልፎ በሰጠው ልጁ በኢየሱስ ተፈጽሟል በሞቱ እና በትንሳኤው በኩል ወደ ተስፋይቱ ምድር መንገድ ከፍቷል፣ እንባን ወደ ማበስ፣ ቁስልን ወደ መፈወስ፣ ወንድሞችና እህቶች እርቅ በመፍጠር ወደ አዲስ ሕይወት ተሻግረዋል።

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ ለዚህ ​​ታሪካዊ ጉብኝት እግዚአብሔርን እናመስግናለን፣ እናም ለዚያች ምድር እና ለመካከለኛው ምስራቅ መጸለያችንን እንቀጥላለን። በኢራቅ ምንም እንኳን የውድመት እና የጦር መሳሪያዎች ጩኸት ቢኖርም የአገሪቱ እና የተስፋዋ ተምሳሌት የሆነው የዘንባባ ዛፍ ማደጉን እና ፍሬ ማፍራት ቀጥሏል። ስለዚህ ለወንድማማችነት ድምጻችንን እያሰማን ፍሬያማ እንዲሆን ማድረግ ይኖርብናል። ሰላም የሆነው እግዚአብሔር የወደፊቱን የወንድማማችነት አንድነት ለኢራቅ ፣ ለመካከለኛው ምስራቅ እና ለመላው ዓለም ይስጥልን።

10 March 2021, 12:44