ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዘንድ ጸሎታቸውን አቀረቡ።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ዛሬ ኅዳር 29/2013 ዓ. ም. ተከብሮ የዋለውን ጽንሰታ ለማርያም ዓመታዊ ክብረ በዓል ምክንያት በማድረግ ባሳረጉት ቅዳሴ ስነ-ሰርዓት የሮም ከተማ ነዋሪዎችን እና መላውን የዓለም ሕዝብ በማስታወስ ጸሎታቸውን ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዘንድ አቅርበዋል። 

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

የጎርጎሮሳውያኑን የቀን አቆጣጠር በምትከተል ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ዘንድ ኅዳር 29/2013 ዓ. ም. ጽንሰታ ለማርያም ዓመታዊ ክብረ በዓል ተከብሮ መዋሉ ታውቋል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በቫቲካን ከሚገኝ መኖሪያቸው ተጉዘው፣ በሮም የሰዓት አቆጣጠር ከጠዋቱ አንድ ሰዓት ላይ በሮም ከተማ፣ ስፔን አደባባይ ወደሚገኝ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መንፈሳዊ ሐውልት ፊት ከደረሱ በኋላ ነጭ የጽጌረዳ አበባ ጉንጉን ካስቀመጡ በኋላ ጸሎት አድርሰዋል። ከዚህ ቀደም ይህ የጸሎት ስነ-ስርዓት በርካታ ምዕመናን በሚገኙበት የከሰዓት በኋላ ዝግጅት ላይ የሚከናወን ቢሆንም የዘንድሮ ግን በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ጠዋት በማለዳ ጥቂት ምዕመናን ብቻ በተገኙት መከናወኑ ታውቋል። ቅዱስነታቸው ከዚህ ስነ-ስርዓት ቀጥለው በሮም ከተማ ውስጥ ወደሚገኝ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ታላቁ ባዚሊካ በመሄድ የሮም ከተማ ሕዝብ ጠባቂ ወደ ሆነች እመቤታችን ዘንድ ጸሎት አቅርበው የመስዋዕተ ቅዳሴ ስነ-ስርዓት ከፈጸሙ በኋላ ወድ ቫቲካን መኖሪያቸው በሰላም ተመልሰዋል።      

08 December 2020, 15:47