ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ባደረጉበት ወቅት ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ባደረጉበት ወቅት 

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በአስቸጋሪ ጊዜያት ለመጸለይ በጭራሽ አትፍሩ አሉ!

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ዘወትር ረቡዕ እለት በቫቲካን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ የሚታወቅ ሲሆን በእዚህ መሰረት ቅዱስነታቸው በሕዳር 30/2013 ዓ.ም ባደረጉት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ በአስቸጋሪ ጊዜያት ለመጸለይ በጭራሽ አትፍሩ ማለታቸው ተገልጿል።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያደረጉትን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አሰናድተነዋል ተከታተሉን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

በጸሎት ዙሪያ ላይ የጀመርነው አስተንትኖ ዛሬም እንቀጥላለን። የክርስቲያን ጸሎት ሙሉ ሰው ያደርገናል - እኛ የምንጸልየው እንደ ሰው ነው፣ እኛ ማን እንደሆንን በማሰብ እንጸልያለን - ጸሎታችን ምስጋና እና ልመናን ያካትታል። በእውነቱ  ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እንዲጸልዩ ሲያስተምር ፣ እርሱ ያስተማረው “አባታችን ሆይ” የሚለውን ጸሎት ነበር ፣ ስለዚህ እኛ በልጅነት መንፈስ እምነት ግንኙነት ውስጥ እራሳችንን ከእግዚአብሄር ጋር እንድናገናኝ እና ሁሉንም ጥያቄዎቻችንን እንድንጠይቀው ይፈልጋል። እግዚአብሔርን ከፍተኛ የሆኑ ስጦታዎች እንዲሰጠን እንለምናለን-ስሙ በሰው ዘንድ እንዲቀደስ፣ መንግሥቱ እንዲመጣ፣ ፈቃዱ በዓለም ውስጥ እንዲፈጸም እንጸልይ። የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ ይህንን በተመለከተ እንዲህ በማለት ያስታውሰናል “በእነዚህ ልመናዎች ውስጥ ተዋረድ አለ - በቅድሚያ ከእዚያም ለአቀባበሉ ስለሚያስፈልገው ሁሉና ከእርሱም ጋር ለመተባበር መደረግ ስላለበት ነገር እንጸልያለን” (የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ ቁ.  2632)።  ነገር ግን “አባታችን ሆይ” በሚለው ጸሎት ውስጥ እንዲሁ ዕለታዊ የሆኑ ስጦታዎች እና እንደ “ዕለታዊ እንጀራ” ላሉት በጣም ወሳኝ የሆኑ ነገሮችን እንዲሰጠን እንጸልያለን - ይህም ማለት ጤና ፣ ቤት ፣ ሥራ ፣ የዕለት ተዕለት ነገሮችን ማለት ነው፣ እንዲሁም ቅዱስ ቁርባን የምንጠይቅ ሲሆን ይህም በክርስቶስ ውስጥ ለሕይወት አስፈላጊ ነው - ለኃጢአት ይቅርታ እንደምንጸልይ - ይህም የዕለት ተዕለት ነገር ነው። ይቅርታን ሁል ጊዜ እንፈልጋለን - እናም ስለዚህ በግንኙነታችን ውስጥ ሰላም እንዲኖር እንማጸናለን፣ በመጨረሻም በፈተናዎች ውስጥ እንደሚረዳን እና ከክፉ ነፃ እንዲያደርገን እንማጸናለን።

ይህንን ዝግጅት ከእዚህ በታች ያለውን ተጫወት የሚለውን ምልክት በመጫን ማዳመጥ ትችላላችሁ!

መጠየቅ እና መለመን። እነዚህ ነገሮች በጣም ሰብዓዊ የሆኑ ነገሮች ናቸው። የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ በድጋሚ እንዲህ ይለናል “በልመና ጸሎት ከእግዚአብሄር ጋር ያለንን ግንኙነት ማወቃችንን እንገልጻለን። እኛ የራሳችን መገኛ ያልሆንን ፍጡራን ነን፣ የክፉ ዕጣ ሆነ የፍጻሜያችን ጌቶች አይደለንም። እንደ ክርስቲያኖች ከአባታችን የራቅን መሆናችንን የምናውቅ ኃጢአተኞች ነን። ስለዚህ ልመናችን ወደ እርሱ መመለስ ነው” (የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ ቁ. 2629)።

አንድ ሰው መጥፎ ነገሮችን ስላደረገ መጥፎ ስሜት ከተሰማው - እሱ ኃጢአተኛ ነው - አባታችን ሆይ የሚለውን ጸሎት ሲጸልይ ወደ ጌታ ይቀርባል። አንዳንድ ጊዜ ምንም ነገር እንደ ማያስፈልገን፣ ለራሳችን በቂ እንደሆንን እና በጣም በተሟላ ደረጃ ራሳችንን መቻል እንችላለን በማለት በእዚህ መልኩ አምነን እንኖራለን። አንዳንድ ጊዜ ይህ ይከሰታል! ነገር ግን ይዋል ይደር እንጂ ይህ ቅዤት ይጠፋል። የሰው ልጅ መሆን ማለት ልመና ማቀረብ ማለት ነው፣ እርሱም አንዳንድ ጊዜ ጩኸት ይሆናል፣ ብዙ ጊዜም ይታገዳል። መዝሙረ ዳዊት እንደ ሚለው ነፍስ ደረቅና የተጠማች ምድር ትመስላለች ( መዝ 63 2)። ሁላችንም በሕይወታችን ፣ ይብዛም ይነስም የሀዘን ወይም የብቸኝነት ጊዜ ያገጥመናል። መጽሐፍ ቅዱስ በበሽታ ፣ በፍትሕ መጓደል ፣ በጓደኞች ክህደት ወይም በጠላቶች ዛቻ የተጠቃውን የሰው ልጅ ሁኔታ ማሳየት አያፍርም። አንዳንድ ጊዜ ሁሉም ነገር የተደመሰሰ ይመስላል ፣ እስከ አሁን የኖርነው ሕይወት በከንቱ እንደ ሆነ ሁኖ የሚሰማን ጊዜ ይኖራል። እናም እነዚህን በሚመስሉ የመጨረሻ ሁኔታዎች ውስጥ አንድ መውጫ መንገድ ብቻ አለ ጩኸት ፣ ጸሎት “ጌታ ሆይ እርዳኝ!” ብሎ መናገር። ጸሎት በጨለማ ውስጥ የብርሃን ፍንጮችን ይከፍታል። “ጌታ ሆይ እርዳኝ!” ማለት በራሱ መንገድ ይከፍታል፣ መንገዱን ያሳያል።

እኛ የሰው ልጆች ከፍጥረታት ሁሉ ጋር ይህንን ለእርዳታ የሚደረገውን ጩኸት እናጋራለን። በዚህ ወሰን በሌለው አጽናፈ ዓለም ውስጥ እኛ ብቻ የምንጸልይ አይደለንም፣ እያንዳንዱ የፍጥረት አካል በእግዚአብሔር ምኞት የተቀረጸ ነው። ቅዱስ ጳውሎስም በዚህ መንገድ ገልጧል። እርሱ እንዲህም ይላል “እስከ አሁን ድረስ ፍጥረት ሁሉ በምጥ ጊዜ እንዳለው ሥቃይ በመቃተት ላይ እንደሚገኝ እናውቃለን። እርሱ ብቻ ሳይሆን፣ የመጀመሪያውን የመንፈስ ፍሬ ያገኘን እኛ ራሳችን የሰውነታችን ቤዛ የሆነውን ልጅነታችንን በናፍቆት እየተጠባበቅን በውስጣችን እንቃትታለን” (ሮሜ 8፡22-24)። የፍጥረታት ሁለገብ ጩኸት በውስጣችን ይሰማናል -የዛፎች ፣ የዐለቶች ፣ የእንስሳት… ወዘተ፣ ሁሉም ነገር ፍጻሜውን ለማግኘት ይናፍቃል። ይህንን በተመለከተ ተርቱሊያን እንዲህ ሲል ገልጾታል “እያንዳንዱን ፍጡር ይጸልያል፣ እንስሳት እና አራዊት ይጸልያሉ፣ ጉልበቶቻቸው ሁሉ ይንበረከካሉ፣ ከጉዞዎቹ ወይም ከጉድጓዶቹ ሲወጡ አንገታቸውን ወደ ሰማይ ከፍ ሲያደርጉ እና አፋቸውን ሳይዘጉ ሲቀሩ እንደ ልማዶቻቸው ጩኸታቸውን ያስተጋባሉ። ወፎቹም እንኳ ሳይቀሩ ልክ እንደበረሩ ወደ ሰማይ ይወጣሉ እና የመስቀል ቅርጽ ያላቸው የሚመስሉ ክንፎቻቸውን ይዘረጋሉ፣ እንደ ጸሎት የሚመስል ነገር ይጮኻሉ ” በማለት ገልጾታል። ይህ ቅዱስ ጳውሎስ “ፍጥረት ሁሉ ይቃትታል ፣ ይጸልያል” በሚለው ላይ አስተያየት ለመስጠት የተጠቀመበት ግጥማዊ አገላለጽ ነው። እኛ ግን በንቃተ ህሊና መጸለይ ፣ ወደ አብ መዞራችንን ማወቅ እና ከአብ ጋር ወደ ውይይት ለመግባት የምንችል ልዩ ፍጥረት መሆናችንን እንገነዘባለን።

ስለዚህ ፣ መጸለይ አስፈላጊ ሆኖ ከተሰማን ማፈር የለብንም ። እናም በተለይም በተቸገርንበት ጊዜ እንለምን። ኢየሱስ ከጌታው ጋር ስለሚሠራው ሐቀኝነት የጎደለው ሰው ሲናገር “መለመን አፍራለሁ” ብሎ ተናግሮ ነበር።  እናም ብዙዎቻችን ይህ ስሜት አለን፣ መለመን እናፍራለን፣ እርዳታ ለመጠየቅ ፣ አንድ ሰው እንድያደርግልን የሚረዳንን ነገር ለመጠየቅ ፣ ግቡ ላይ ለመድረስ እና እግዚአብሔርን ለመጠየቅ ደግሞ እናፍራለን። በመጸለይ “ጌታ ሆይ ይህ ነገር ያስፈልገኛል” ብሎ መጠየቅ ማፈር የለብንም ፣ "ጌታ ሆይ ፣ በዚህ ችግር ውስጥ ነኝ" ፣ "እርዳኝ!" አባት ወደ ሆነው ወደ እግዚአብሔር የልብ ጩኸታችንን ማቅረብ ይኖርብናል። እናም በደስታ ጊዜያት እንኳን ለማድረግ መማር አለብን፣ ስለ ተሰጠን ነገር ሁሉ እግዚአብሔርን እናመስግን፣ ምንም ዓይነት ነገር አቅልላችሁ አትመልከቱ፣ ሁሉም ነገር ፀጋ ነው። ጌታ ሁል ጊዜ ይሰጠናል ፣ ሁል ጊዜም ፣ እናም ሁሉም ነገር ጸጋ ፣ ሁሉም ነገር ስጦታ ነው። የእግዚአብሔር ጸጋ ነው። ሆኖም ግን በራስ ተነሳሽነት በውስጣችን የሚነሳውን ልመና አናፍን። የጥያቄው ጸሎት ከአቅማችን እና ከፍጥረታት በላይ ሆኖ ሽቅብ ወደ ላይ የወጣል። አንድ ሰው በእግዚአብሔር ማመን እንኳን ሊቸገር ይችላል፣ ነገር ግን በጸሎት አለማመን ከባድ ነው - በቃ በቀላሉ እርሱ አለ፣ እሱ እራሱን እንደ ጩኸት ለእኛ ያቀርባል፣ እናም ሁላችንም ይህንን የውስጠ-ድምጽ ማስተናገድ አለብን ለረጅም ጊዜ ዝም ሊል ይችላል ፣ ነገር ግን አንድ ቀን ከእንቅልፉ ይነሳል እና ይጮኻል።

ወንድሞች እና እህቶች እግዚአብሔር እንደሚመልስ እናውቃለን። በመዝሙረ ዳዊት መጽሐፍ ውስጥ የእርሱን ጩኸት ከፍ አድርጎ ያቀረበ እና ያልተሰም ጸሎት የለም። እግዚአብሔር ሁል ጊዜ መልስ ይሰጣል-ዛሬ ፣ ነገ ግን እርሱ በማንኛውም ጊዜ ወይም በሌላ መንገድ ይመልሳል። ሁል ጊዜ መልስ ይሰጣል። መጽሐፍ ቅዱስ ስፍር ቁጥር የሌላቸውን ጊዜያት ይደጋግማል-እግዚአብሔር የሚለምኑትን ሰዎች ጩኸት ይሰማል። የተንተባተቡ ጥያቄዎቻችን እንኳን ፣ በልባችን ጥልቅ ውስጥ የቀሩትም ፣ እኛ ደግሞ ለመግለፅ የምናፍርባቸው ፣ አብ ያዳምጣቸዋል። አብ እያንዳንዱን ፀሎት የሚያነቃቃ እና ሁሉንም ነገር የሚቀይር መንፈስ ቅዱስን ሊሰጠን ይፈልጋል። በትዕግስት መጠበቅ ይኖርብናል፣ ሁልጊዜ ትዕግሥት አስፈላጊ ነው። እኛ አሁን በስብከተ ገና ወቅት ውስጥ እንገኛለን፣ በተለምዶ የገናን በዓል የምንጠባበቅበት ወቅት። እየጠበቅን ነው። ይህ በደንብ ሊታይ ይችላል። ነገር ግን ህይወታችን በሙሉ እንዲሁ እየጠበቀ ነው። እናም ጌታ ሁል ጊዜ መልስ እንደሚሰጥ እናውቃለንና ጸሎት ሁል ጊዜም እየጠበቀ ነው። አንድ ክርስቲያን በሚጸልይበት ጊዜ ሞት እንኳን ይንቀጠቀጣል፣ ምክንያቱም የሚጸልይ ሰው ሁሉ ከእርሱ የበለጠ ጠንካራ አጋር እንዳለው ያውቃል - ከሞት የተነሳው ጌታ ከእርሱ ጋር እንደ ሆነ ያውቃል፣  ሞት ቀድሞውኑ በክርስቶስ ተሸንፏል፣ እናም ሁሉም ነገር በእርግጠኝነት የሚመጣበት ቀን ይመጣል ፣ እናም ከእንግዲህ በሕይወታችን እና በደስታችን ላይ ማሾፍ የለብንም።

ጌታን መጠበቅን እንማራለን። ጌታ ሊጎበኘን የሚመጣው በእነዚህ ታላላቅ በዓላት ላይ ብቻ አይደለም - ገና ፣ ፋሲካ - ነገር ግን ጌታ እየጠበቅን ከሆነ በልባችን ቅርበት በየቀኑ ይጎበኘናል። እናም ብዙ ጊዜ ጌታ ቅርብ መሆኑን ፣ በራችንን እንደሚያንኳኳ እና እሱ እንዲያልፍ አናድርገው። ቅዱስ አጎስጢኖስ “እግዚአብሔር አልፎ ሲሄድ ያስፈራኛል፣ ያልፋል ብዬ እፈራለሁ አላስተውለውምም” ብሎ ተናግሮ ነበር። ጌታም ያልፋል ፣ ጌታ ይመጣል ፣ ጌታ ያንኳኳል። ነገር ግን ጆሮዎቻችን በሌሎች ጫጫታዎች የተሞሉ ከሆነ የጌታን ጥሪ ማዳመጥ ይሳናቸዋል።

ወንድሞች እና እህቶች በትዕግስት መጠበቅ በራሱ ጸሎት ነው!

09 December 2020, 12:26

በቅርብ ጊዜ ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር የተደረገው ግንኙነት

ሁሉንም ያንብቡ >