ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ውስጥ መስዋዕተ ቅዳሴ ባሳረጉበት ወቅት ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ውስጥ መስዋዕተ ቅዳሴ ባሳረጉበት ወቅት  

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ለሟች ካርዲናሎች እና ጳጳሳት መስዋዕተ ቅዳሴ አሳረጉ!

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ባለፈው ሐሙስ ጥቅምት 26/2013 ዓ.ም ባለፉት 12 ወራት ውስጥ ከእዚህ ዓለም በሞት ለተለዩ ስድስት ካርዲናሎች እና ለ 163 ጳጳሳት በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ መስዋዕተ ቅዳሴ ማሳረጋቸው የተገለጸ ሲሆን በዚህ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽ ምክንያት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በተወሰዱ የጤና እና የደኅንነት እርምጃዎች ምክንያት ጥቂት ምዕመናን በተገኙበት እና በተሳተፉበት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ቅዱስነታቸው አስምተው የነበረው ስብከት “እኔ ትንሳኤ እና ሕይወት ነኝ” በሚለው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ላይ መሰረቱን ያደረገ እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን እኛ ክርስቲያኖች ከሞት በኋላ ሕይወት እንዳለ በሚገባ እናምናለን ማለታቸው ተገልጿል።

አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ትንሣኤ እና ሕይወት

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያደረጉት ስብከት “እኔ ትንሳኤ እና ሕይወት ነኝ” የሚሉት የኢየሱስን ቃላት በማስታወስ አልዓዛርን ከሞት እንደ ተነሳ በሚገልጸው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ላይ መሰረቱን ያደረገ ነበር። እንዲሁም ማርታ በእርሱ ማለትም በክርስቶስ ላይ ያላትን እምነት የገለጸችበትና “አዎን ጌታ ሆይ ወደ ዓለም የሚመጣው ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆንህ አምናለሁ” ብላ ስለ ክርስቶስ መመስከሯን ቅዱስነታቸው አክለው ገልጸዋል።

“የኢየሱስ ቃላት” ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት እንዳሉት ወደፊት በሚመጣው ትንሣኤ የማርታን ተስፋ በማለምለም  እኛም በሙታን ትንሳኤ እንድናምን “አሁን በሕይወታችን ውስጥ ምሥጢራዊ በሆነ አኳኋን እየሠራ” ያለ እውነታ “በትንሣኤው እንድናምን” ይጋብዘናል ብለዋል። በሞት ፊት ፣ ሀዘን እና ግራ መጋባት ያጋጥመናል። ነገር ግን በኢየሱስ መገለጥ የማይታዩ እውነታዎችን ማስተዋል እና ነገሮችን ከዘለአለም ብርሃን አኳያ ማየት እንችላለን ብለዋል።

ነገሮችን ከምድራዊ እይታ አኳያ ብቻ የሚያዩ ሰዎች የሚወዳቸውን የእግዚአብሔርን ዕቅድ መረዳት አይችሉም በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ነገሮችን ከእግዚአብሄር እይታ አንጻር ስናይ ግን ሞት ከእንግዲህ “እንደ መጥፎ አጋጣሚ” አድርገን አንቆጥረውም፣ ይልቁንም ሐሳቡ ከሐሳባችን እጅግ በጣም የተለየውን የጌታን መለኮታዊ ጥበቃ በትግባር ለማየት እንችላለን ብለዋል።

ለሙታን መጸለይ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እንዳሉት “ባለፈው ዓመት ከእዚህ ዓለም በሞት ለተለዩት ካርዲናሎች እና ጳጳሳት ይህንን መስዋዕተ ቅዳሴ በማደረግ በጸሎት ስናስታውሳቸው የሕይወታቸውን ምሳሌ በትክክል እንድናጤን ጌታ እንዲረዳን እንጠይቃለን” ብለዋል። እንዲሁም “አልፎ አልፎ የምንፈራውን እና ሞት የሁሉም ነገር ማብቂያ ነው በሚል ሐሳብ ተነሳስተን ሐዘን ውስጥ እንዳንገባ እና የእዚህ ዓይነት ሐስተሳሰብ ከሕይወታችን ማስወገድ እንችል ዘንድ እንዲረዳን እግዚአብሔርን ልንማጸን ይገባል ያሉት ቅዱስነታቸው ሁሉም ሰዎች ሞትን እንደ ሚፈሩ ተናግረዋል። አማኞች በሙሉ ከሞት በኋላ ትንሣኤ እንዳለ የሚገልጸውን እምነታቸውን ማደስ ይኖርባቸዋል ብለዋል። ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ አጥብቀው ሲናገሩ ሞት “የሰው የመጨረሻ እና አጠቃላይ መደምደሚያ አይደለም” ብለዋል። ይልቁንም “እኔ ትንሳኤ እና ህይወት እኔ ነኝ” ብሎ በሚነግረን በጌታ ቃል ሁል ጊዜ መታመን አለብን ብለዋል። በእምነት ተቀባይነትን ያገኙ የኢየሱስ ቃላት ለሞቱት ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን የምናቀርበውን ጸሎት በእውነት ክርስቲያናዊ ያደርጋቸዋል” በማለት አብራርተዋል።

እውነተኛ የሕይወት ራዕይ

ይህ አመለካከት ከእኛ በፊት ስለነበሩት ሰዎች ሕይወት እውነተኛ ፣ “ተጨባጭ” ግንዛቤን ይሰጠናል ፣ እናም “ወደ ምድራዊ የትውልድ አገር ሳይሆን ወደ ተሻለ ሰማያዊ አገር የሚመኝ የሕይወትን ትርጉም እንድንገነዘብ ይረዳናል” በማለት በስብከታቸው አክለው ገልጸዋል።

ስለዚህ ለሙታን መጸለይ በዚህ ምድራዊ ሕይወት ውስጥ ለሚቀሩ ሰዎችም ጠቃሚ ነው ሲሉ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በስብከታቸው የተናገሩ ሲሆን እነሱ እውነተኛ የሕይወት ራዕይ በውስጣችን እንዲነሳሳ ያደርጋሉ፣ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት በጽናት መዋጋት ያለብንን ፈተናዎች ትርጉም ለእኛ ያሳዩናል ፤ ልባችንን ለእውነተኛ ነፃነት ይከፍታሉ እናም ያለማቋረጥ የዘላለም ሀብትን እንድንፈልግ ያነሳሱናል ብለዋል።

የሞቱትን ሰዎች ምስክርነት በማስታወስ

ጌታን የሚከተሉ ሰዎች ሕይወታቸውን የሚቀይሱት እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኘውን ለማድረግ በመፈለግ ነው ሲሉ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ስብከታቸውን የቀጠሉ ሲሆን “እናም ስለዚህ ለእግዚአብሄር ፈቃድ በታማኝነት የተሰጡ የሟቹ ካርዲናሎች እና ጳጳሳት ምስክር በአመስጋኝነት እናስታውሳለን። እኛ ስለ እነሱ እንጸልያለን፣ እኛም የእነሱን አርአያ ለመከተል እንጥራለን ”ብለዋል ፡፡

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጌታ “በተለይም በእነዚህ የፈተና ጊዜያት” የጥበብ መንፈሱን በእኛ ላይ ማሳረፉን እንዲቀጥል በጸሎት መትጋት ይኖርብናል ያሉ ሲሆን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን “አይተወንም ፣” ነገር ግን “እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” በማለት ለገባው ቃል ታማኝ በመሆን በመካከላችን ይኖራል ካሉ በኋላ ቅዱስነታቸው ስብከታቸውን አጠናቀዋል።

05 November 2020, 11:23