ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በቫቲካን  

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ፍቅር የአማኞች ሕይወት ምስጢራዊ መሠረት ነው ማለታቸው ተገለጸ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ዘወትር ረቡዕ እለት በቫቲካን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ የሚታወቅ ሲሆን በዚህም መሰረት ቅዱስነታቸው በሕዳር 16/2013 ዓ.ም  ያደረጉት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ጴጥሮስና ዮሐንስም ከተፈቱ በኋላ ወደ ወገኖቻቸው ተመልሰው የካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች ያሏቸውን ሁሉ ነገሯቸው። እነርሱም ይህን በሰሙ ጊዜ ድምፃቸውን በአንድነት ወደ እግዚአብሔር ከፍ አድርገው እንዲህ አሉ፤ “ልዑል ጌታ ሆይ፤ አንተ ሰማይንና ምድርን፣ ባሕርንም፣ በውስጣቸውም የሚኖሩትን ሁሉ ፈጥረሃል፤ በርግጥም ሄሮድስና ጳንጥዮስ ጲላጦስ ከአሕዛብና ከእስራኤል ሕዝብ ጋር በዚህች ከተማ አንተ በቀባኸው በቅዱሱ ብላቴናህ በኢየሱስ ላይ ለማሤር ተሰበሰቡ፤ ይህም የሆነው የአንተ ክንድና ፈቃድ ጥንት የወሰኑት እንዲፈጸም ነው። አሁንም ጌታ ሆይ፤ ዛቻቸውን ተመልከት፤ ባሪያዎችህም ቃልህን በፍጹም ድፍረት መናገር እንዲችሉ አድርጋቸው። ለመፈወስ እጅህን ዘርጋ፤ በቅዱሱ ብላቴናህም በኢየሱስ ስም ድንቅና ታምራት አድርግ።” ከጸለዩም በኋላ የነበሩበት ስፍራ ተናወጠ፤ ሁሉም በመንፈስ ቅዱስ ተሞሉ፤ የእግዚአብሔርንም ቃል በድፍረት ተናገሩ (የሐዋርያት ሥራ 4፡23 30) በተሰኘው የመጀመሪያዎቹ አማኞች ጸሎት ላይ መሰረቱን ያደረገ አስተምህሮ የነበረ ሲሆን ፍቅር የአማኞች ሕይወት ምስጢራዊ መሠረት ነው ማለታቸው ተገልጿል።

ይህንን ዝግጅት ከእዚህ በታች ያለውን ተጫወት የሚለውን ምልክት በመጫን ማዳመጥ ትችላላችሁ!

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያደረጉትን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አሰናድተነዋል፣ ተከታተሉን።

ውድ ወንድሞች እና እህቶች እንደምን አረፈዳችሁ!

ቤተክርስቲያን በዓለም ውስጥ ያደረገቻቸው እርምጃዎች የተጀመሩት በቅድሚያ በጸሎት በመጠመድ ነበር። ሐዋርያዊ ጽሑፎች እና የሐዋርያት ሥራ ታላቅ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል እንደ ሚነግሩን በእንቅስቃሴ ላይ ያለች ንቁ ቤተክርስቲያን ምስልን ይሰጡናል ፣ ሆኖም በጸሎት መንፈስ የተሰበሰበው ማሕበረሰብ ለሚስዮናዊ ተግባር መሠረትን እና ተነሳሽነትን አግኝቷል። የጥንቱ የኢየሩሳሌም ማህበረሰብ ምስል ለሌሎች ክርስቲያናዊ ልምዶች ሁሉ ዋቢ ነጥብ ነው። ወንጌላዊው ሉቃስ በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ውስጥ “እነርሱም በሐዋርያት ትምህርትና በኅብረት፣ እንጀራውንም በመቍረስና በጸሎት ይተጉ ነበር” (የሐዋርያት ሥራ 2፡42) በማለት ገልጾታል።የቤተክርስቲያን ሕይወት አራት አስፈላጊ ባህሪያትን እዚህ ጋር እናገኛለን - የሐዋርያትን ትምህርት ማዳመጥ ፣ የጋራ መከባበርን መጠበቅ፣ እንጀራ መቁረስ እና ጸሎት የተሰኙት ናቸው። እነሱ ከክርስቶስ ጋር በጥብቅ ከተዋሃድን የቤተክርስቲያኗ ህልውና ትርጉም እንዳለው ያስታውሱናል። ስብከት እና ትምህርተ ክርስቶስ የመምህሩን ቃላቶች እና ድርጊቶች ይመሰክራሉ፣ የማያቋርጥ የወንድማማችነት ኅብረት መፈለግ ነገሮችን በተናጥል ከማድረግ ይጠብቀናል፣ እንጀራውን በምንቆርስበት ወቅት ደግሞ በመካከላችን ያለውን የኢየሱስን ምስጢረ ቁርባን ያሟላል እርሱ በጭራሽ ከእኛ አይለይም፣ እርሱ ከእኛ ጋር አብሮ ይራመዳል። እናም በመጨረሻም ጸሎት ከአብ ጋር የምንወያይበት፣ በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ክርስቶስ ጋር የምንወያይበት ስፍራን ያዘጋጃል።

ከእነዚህ ነገሮች ውጭ በቤተክርስቲያኗ ውስጥ ያለው ማንኛውም ነገር እና እድገት መሰረት የለውም ፤ እሱ በአሸዋ ላይ እንደተሰራ ቤት ነው (ማቴዎስ 7፡24-27) ። ቤተክርስቲያንን የፈጠረው እግዚአብሄር ነው እንጂ ቤተክርስቲያን የእኛ ጩኸት ወጤት አይደለችም። ጥረታችንን ትርጉም ባለው መልኩ የሚሞላው የኢየሱስ ቃል ነው። የዓለምን መፃኢ ዕድል የምንገነባው በትህትና ነው።

የሐዋርያት ሥራ መጸሐፍን በማንበብ ከዚያ የጸሎት ስብሰባዎች የወንጌል ስርጭት ኃይለኛ እንዴት ሊመነጭ እንደሚችል እናገኛለን ፣ በጸሎት ውስጥ የሚሳተፉ በእውነቱ የኢየሱስን መኖር የሚለማመዱ እና በመንፈሱ የሚነኩ ሰዎች እንደ ሆኑም እንመለከታለን። የመጀመሪው የክርስቲያን ማህበረሰብ አባላት - ምንም እንኳን ይህ ሁልጊዜ ለእኛም ዛሬም ቢሆን የሚሠራ ቢሆንም - ከኢየሱስ ጋር የመገናኘታችን በእርሱ እርገት የተነሳ በእዚያው የሚያበቃ ሳይሆን ነገር ግን በህይወታችን እንደሚቀጥል ይሰማናል። ጌታ የተናገረውን እና ያደረገውን በመጥቀስ ፣ ከእሱ ጋር ወደ ህብረት ለመግባት በመጸለይ ሁሉም ነገር ህያው ይሆናል። ጸሎት ብርሃንን እና ሙቀትን ያስገኛል የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ በጋለ ስሜት ይሰጠናል።

በዚህ ምክንያት የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ይህንን በተመለከተ ጉልህ የሆነ አገላለፅን በመጠቀም - “መንፈስ ቅዱስ ... በጸሎት አማካይነት ቤተክርስቲያንን ወደ እውነት ሙላት ይመራታል፣ እንዲሁም በቤተክርስቲያን ሕይወት ምስጢራትና ተልዕኮ ውስጥ የማይመረመረውን የክርስቶስን ምስጢር የሚገልጹ አዳዲስ አሰራሮችን እንድትከተል ቤተክርስቲያንን ያነሳሳታል። እነዚህ መገለጫዎች በይበልጥ የሚዳብሩት በታላላቆቹ ስርዓተ አምልኮ ሕይወት በቤተክርስቲያኗ ሕይወት፣ በቅዱስ ቁርባን እና መንፈሳዊ ወጎችን በተከተለ ተልእኮ ውስጥ በመሥራት ነው”( የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ቁ. 2625)። ይህ በቤተክርስቲያን ውስጥ መንፈስ ቅዱስ የሚያከናውነው ተግባር ነው -ኢየሱስን እንድናስታውስ ያደርገናል። ነገር ግን ይህ እንደ ለአንድ ለማስታወስ የሚረዳ ቀመር አይደለም። ክርስቲያኖች በተልእኮ ጎዳናዎች ላይ እየተራመዱ ሲሄዱ ኢየሱስ ሕያው እንደ ሆነ ያስታውሱናል፣ እናም ከእሱ፣ ከመንፈሱ የተነሳ እርሱን ለማወጅ እና ለማገልገል ወደ ፊት እንዲሄዱ “ይገፋፋቸዋል” ። በጸሎት ውስጥ ክርስቲያኖች እያንዳንዱን ሰው በሚወደው እና ለእያንዳንዱ ሰው ወንጌል እንዲሰበክ በሚፈልግ የእግዚአብሔር ምስጢር ውስጥ ራሳቸውን ይጠመዳሉ። እግዚአብሔር ለሁሉም ሰው አምላክ ነው፣ በኢየሱስ ስም ውስጥ የመለያያ ግድግዳዎች ሁሉ በትክክል ተደርምሰዋል - ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው እርሱ ሰላማችን ነው “ሁላችንንም አንድ ያደረገን” እርሱ ነው (ኤፌ 2፡14) ይለናል።

በዚህ መንገድ በመጀመሪያው ዘመን የነበረችው ቤተክርስቲያን ሕይወት ቀጣይ እንዲሆን፣ የምልዓቶች ፣ የኅብረት እና የግል ጸሎት ጊዜያት ተከታታይ የልብ ምት ነበራቸው። እናም ጉዞውን ለጀመሩ ሰባኪዎች ጥንካሬን የሰጠው እና ለኢየሱስ ፍቅር ለመስበክ በአስቸጋሪ ሁኔታ በባህር ላይ በመርከብ ሲጓዙ የነበሩ ሰዎች አደጋዎችን መጋፈጥ ያስቻላቸው እና ራሳቸውን ለውርደት እንዲያዘጋጁ ያደረገው መንፈስ ቅዱስ ነው።

እግዚአብሔር ፍቅርን ይሰጣል ፍቅርንም ይጠይቃል። ይህ የአማኙ አጠቃላይ ሕይወት ሚስጥራዊ ሥር መሰረት ነው። በጸሎት ፣ የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች እና እኛም እንዲሁ ፣ ከብዙ መቶ ዘመናት በኋላ የመጣን - ሁላችንም ተመሳሳይ ተሞክሮ እንኖራለን። መንፈስ ቅዱስ ሁሉንም ነገር ያነሳሳል። እናም ለጸሎት ጊዜ ለመስጠት የማይፈራ እያንዳንዱ ክርስቲያን “አሁን በሥጋ የምኖርበት ሕይወት በወደደኝና ራሱን ለእኔ በሰጠው በእግዚአብሔር ልጅ ላይ በማመን እኖራለሁ  ”(ገላ 2፡20) የሚለውን የሐዋርያው ​​ጳውሎስን ቃላት የራሱን ቃል ማድረግ ይችላል። የእነዚህን ቃላት አጠቃላይ እውነት የምንለማመደው በስግደት በሚደረግ የዝምታ ጸሎት ብቻ ነው። ለመመሥከር እና ለተልእኮ ጥንካሬን የሚሰጠው ሕያው የሆነው የመንፈስ ቅዱስ ነበልባል ነው።

25 November 2020, 12:26

በቅርብ ጊዜ ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር የተደረገው ግንኙነት

ሁሉንም ያንብቡ >