Pope's Angelus prayer Pope's Angelus prayer 

ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ፣ “መልካም እረኛ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ መመካት ያስፈልጋል”።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እሁድ ጳግሜ 1/2012 ዓ. ም ያቀረቡትን የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ ካጠናቀቁ በኋላ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተገኙት የሮም ሀገረ ስብከት ምዕመናን፣ የቁምስና መንፈሳዊ ማኅበራት እና እንቅስቃሴዎች አባላትን እንዲሁም ከተለያዩ አገራት ለመጡ ነጋዲያን ሰላምታቸውን አቅርበውላቸዋል።

ከእነዚህም መካከል በሮም ከተማ የሚገኝ የሰሜን አሜርካ ከፍተኛ የዘርዓ ክህነት ተማሪዎች፣ የሉቢያና እና የስሎቬኒያ ዘርዓ ክህነት ተማሪዎች የሚገኙበት መሆኑ ታውቋል። ቅዱስነታቸው ለእነዚህ እና ከሌሎች አካባቢዎች ለመጡት ወጣቶች ባቀረቡት የማበረታቻ ቃላቸው፣ የማዕዘን ራስ እና በጎ እረኛ በሆነው በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ እምነታቸውን እንዲያሳድሩ አሳስበዋል።

በተጨማሪም ከጣሊያን፣ ሴና ከተማ ወደ ሮም የመጡ ሴት አትሌቶችን እና ለበጎ ሥራ አገልግሎት እርዳታን ለማሰባሰብ በሚል ዓላማ የተሰማሩ ብስክሌተኞችን አመስግነው ይህን ሥራቸውን በደስታ እና በእምነት ወደ ፊት እንዲያራምዱት አደራ ብለዋል።

ቅዱስነታቸው ከዚህም በተጨማሪ ከፖላንድ፣ ከሊባኖስ፣ ከፈረንሳይ፣ ከሜክስኮ እና ከሌሎች አገሮች ለመጡት ምዕመናን በሙሉ ሰላምታቸውን አቅርበው መልካም ዕለተ ሰንበትን ከተመኙ በኋላ ምዕመናኑ በጸሎታቸው እንዲያስታውሷቸው አደራ ብለው የዕለቱን ንግግራቸውን ደምድመዋል።       

07 September 2020, 11:25