ር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ፣ አንድነትን የምናሳድግ እውነተኛ ነቢያት መሆን ይኖርብናል አሉ።

የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ ትናንት ሰኔ 22/2012 ዓ. ም. የቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ ዓመታዊ በዓል ተክብሮ መዋሉ ሲታወስ በዕለቱ የቀረበውን የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት የመሩት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በስብከታቸው አንድነትን የምንገነባ እውነተኛ ነቢያት መሆን ይኖርብናል ማለት ታውቋል። ክቡራት እና ክቡራን፣ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በትናንትናው ዕለት ያሰሙትን ስብከት ትርጉም ሙሉ ይዘቱን ከዚህ ቀጥሎ እንደሚከተለው አቅርበንላችኋል፥ 

የቫቲካን ዜና፤  

“የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ፣

በዛሬው ዕለት የሮም ከተማ ባልደረባ የሆኑት፣ የቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ ክብረ በዓል እናከብራለን። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በሰማዕነት በሞተበት አካባቢ እና በተቀበረበት ሥፍራ ላይ ሆነን ጸሎታችንን ማቅረብ መቻላችን ትልቅ ስጦታ ነው። የዛሬው መስዋዕተ ቅዳሴያችን ከበዓሉ ጋር የማይገናኝ ታሪክ እንድናስታውስ አድርጎናል። ከበርካታ ዘመናት በፊት ሐዋርያው ጴጥሮስ ከሞት ነጻ መውጣቱን ያስታውሰናል። ሐዋርያው ጴጥሮስ ተይዞ መታሠሩን፣ ቤተክርስቲያንም ለሕይወቱ በመጨነቅ ሳታቋጥ ስትጸልይለት መቆየቷን፣ በኋላም መልአክ ከሰማይ ወርዶ ነጻ እንዳወጣው ከመጽሐፍ ቅዱስ እናነባለን። (ሐዋ. ሥራ 12: 1-11) ከዓመታት በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ በሮም በታሰረበት ጊዜም ቤተክርስቲያን ለቅዱስ ዮሴፍ መጸለይ አላቋረጠችም። ቢሆንም በዚህ ጊዜ ከሞት ሊተርፍ አልቻለም። “አስቀድሞ ከታሰረበት ነጻ መውጣት ከቻለ በሮም በታሰረ ጊዜ ለምን ነጻ ሊወጥ አልቻለም?” የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል።

ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ ነጻ ሊወጣ ያልቻለበት ምክንያት በሕይወት ውስጥ ለመንገዳችን ብርሃን የሚሆን ጸጋ ስለነበር ነው። እግዚአብሔር ለቅዱስ ጴጥሮስ ብዙ ጸጋዎችን በመስጠት ከሰይጣን ወጥመድ ነጻ እንዲወጣ አድርጎታል። እግዚአብሔር ይህን ታላቅ ሥራ ለእኛም ያደርግልናል። እኛ ብዙን ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ፊት የምንቀርበው የእርሱን እርዳታ ስንፈልግ ነው። ነገር ግን እግዚአብሔር አርቆ በማሰብ የእርሱን ስጦታ ብቻ ሳይሆን የስጦታዎች ባለቤት የሆነውን እግዚአብሔርን እንድንፈልግ ይጠይቀናል። ወደ እርሱ ዘንድ ይዘን የምንቀርበው ችግሮቻችንን ብቻ ሳይሆን ሙሉ ሕይወታችን እንዲሆን ይፈልጋል። በዚህም ሕይወታችንን የምንሰጥበት ታላቅ ስጦታን ይሰጠናል። በሕይወት ውስጥ ትልቁ ነገር ሕይወትን አሳልፎ መስጠት ነው። ይህ እውነት በሁሉም ዘንድ ሊገለጽ ይችላል፤ ወላጆች ለልጆቻቸው፣ ልጆችም ለወላጆቻቸው እና ለአያቶቻቸው ሕይወትን አሳልፈው ሊሰጡ ይችላሉ። ይህን በምንልበት ጊዜ በቤተሰብ ውስጥ የተረሱ እና ረዳት የሌላቸውን በርካታ የዕድሜ ባለጸጋዎችን ማስታወስ ይቻላል። አረጋዊያን ያለ ረዳት ብቻቸውን መቅረት የዘመናችን አስከፊ ገጽታ ነው። የአዳጊ ሕጻናት ሕይወት ለዕድሜ ባለጸጋዎች የተሰጠ ስጦታ መሆኑን እንዘንጋለን። ራሳችንን ለጋብቻ ሕይወት ወይም ለምንኩስና ሕይወት አሳልፈን እንሰጣልን። በሁሉም አካባቢ፣ በቤትም ሆነ በሥራ አካባቢ ይህ ሲሆን እንመለከታለን። እግዚአብሔር በመስጠት እንዳንታወቅ እና እንድናድግ ይፈልጋል። ማደግም የምንችለይ ራስን ለሌሎች መስጠት ስንችል ብቻ ነው። ራሳችንን ለሌሎች የምንሰጥ ከሆነ በእርግጥ ማደግ እንችላለን። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስን ብንመለከት፣ ቅዱስ የተባለው ከእስር ነጻ ስለ ተለቀቀ አይደለም። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ቅዱስ የተባለው ሕይወቱን ለሞት አሳልፎ ስለ ሰጠ ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ ለሞት ራሱን አሳልፎ የሰጠው ቦታ ዛሬ ለእኛ የመልካም ተስፋ ሥፍራ ሆኖ አግኝተናዎናል።  

እግዚአብሔርንም የምንጠይቀው ይህን ነው፥ ጊዜያዊ ጸጋን ሳይሆን የሕይወት ጸጋን ነው። ዛሬ የተነበበው የወንጌል ክፍል የቅዱስ ጴጥሮስ ሕይወት የተለወጠበትን ውይይት ያስታውሰናል። ኢየሱስም ጴጥሮስን እንዲህ ሲል ጠየቀው፥ “እኔን ማን ትለኛለህ”? አለው። ጴጥሮስም፥ “አንተ መሲህ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” አለው። ኢየሱስም፥ “የዮና ልጅ ስምዖን፣ አንተ የተባረክ ነህ“ አለው (የማቴ. 16፡ 16-17)። ኢየሱስ ጴጥሮስን “የተባረክ” ሲለው “ደስተኛ ነህ” ማለቱ ነበር። ቅዱስ ጴጥሮስ ኢየሱስን “አንተ ሕያው እግዚአብሔር ነህ” ባለው ጊዜ ኢየሱስም “አንተ የተባርክ ነህ” ማለቱን ልናስተውል ይገባል። የተባረከ ሕይወት፣ የደስታ ሕይወት ምስጢር ምንድነው? ኢየሱስ ሕያው አምላክ መሆኑን ማወቅ እና መረዳት ነው። ኢየሱስ በዘመናት ታሪክ ውስጥ ትልቅ ስፍራ እንዳለው ማወቅ ወይም ስለ ተናገራቸውና ስላደረጋቸው ነገሮች አድናቆት መስጠት ይህን ያህል ጠቃሚ አይደለም። ትልቁ እና ዋናው ነገር፣ በሕይወቴ ውስጥ ለኢየሱስ የምሰጠው ቦታ ነው፤ በልቤ ውስጥ ለኢየሱስ የምሰጠው ሥፍራ ነው። ጴጥሮስም ኢየሱስ ስለ እርሱ እንዲህ ሲል ሰማዉ፥ አንተ አለት ነህ፤ በዚህች የመሠረት ድንጋይ ላይ ቤተክርስቲያኔን እሠራለሁ (የማቴ. 16፡ 18)። “ጴጥሮስ” ብሎት አልጠራውም፤ “አለት” ብሎት ጠራው እንጂ። ምክንያቱም ቅዱስ ጴጥሮስ መሠረቱ የማይነቃነቅ ጠንካራ እና ታማኝ ሰው ስለነበር ነው። ይሁን እንጂ ጴጥሮስ ከዚያ በኋላ ብዙ ስህተቶችን ሠርቷል፣ ኢየሱስን እስከ መካድ ደርሷል። ቢሆንም ሕይወቱን በራሱ ላይ በመተማመን ሳይሆን ስጋውን እና ደሙን በሰጠው በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነው የመሰረተው። (የማቴ. 16፡ 17)። ለቅዱስ ጴጥሮስ መሠረቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ ሁሉ ነገር እንደማይጠቅመው በተገነዘበ ጊዜ ኢየሱስን ብቻ የሕይወቱ መሪ አደርገው። ሕይወቱን በሙሉ ለወንጌል አገልግሎት አሳልፎ የሰጠውን ሐዋርያው ጳውሎስንም በተመሳሳይ መንገድ እንገልጸዋለን።

ዛሬ በእነዚህ ሁለቱ ሐዋርያት ፊት ቆመን ራሳችንን መጠየቅ ያለብን ጥያቄ “ሕይወቴን እንዴት እመራለሁ? ለጊዜያዊ ፍላጎቶች ብቻ ነው ወይስ ራሴን አሳልፌ እንድሰጥ በሚያደርገኝ በኢየሱስ ክርስቶስ ነው?” የሚል መሆን አለበት። ሕይወቴን የምመሠርተው በራስ በመመካት ነው ወይስ በሕያው እግዚአብሔር ላይ ነው? እምነቷን በሙሉ በእግዚአብሔር ላይ ያደረገች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በዕለታዊ ሕይወታችን እግዚአብሔርን እንድናስቀድም፣ ሕይወታችንን ለሌሎች መስጠት እንድንችል ታግዘን በማለት ጸሎታችንን እናቀርባለን”።                

30 June 2020, 18:15