ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “2020 ዓ.ም ተስፋችን እና ሰላም የሚለመልምበት ዓመት ያድርግልን” አሉ!

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “2020 ዓ.ም ተስፋችን እና ሰላም የሚለመልምበት ዓመት ያድርግልን” አሉ!

የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የዓለማችን የማኅበረሰብ ክፍሎች ዘንድ 2019 ዓ.ም ተጠናቆ የ2020 ዓ.ም አዲስ ዓመት በታኅሳስ 22/2012 ዓ.ም መጀመሩ ይታወሳል። በተመሳሳይ መልኩ በዚሁ በጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር የ2020 ዓ.ም የአዲስ አመት መጀመሪያ ቀን ላይ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ ከአዲስ አመት በዓል ባሻገር ስለ እመቤታችን እጅግ ቅድስት ድንግል ማርያም ከተደነገጉ አራት የእምነት እውነቶች (ዶግማዎች) መካከል በቀዳሚነት የሚገኘውና እ.አ.አ በ250 ዓ.ም አከባቢ ላይ የተደነገገው “እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ እናት ” መሆኑዋን በመግለጽ የሚከበረው ዓመታዊ በዓል በታኅሳ 22/2012 ዓ.ም ተክብሮ ማለፉ የሚታወስ ሲሆን ይህንን በዓል ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ካሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ በመቀጠል፣ ይህንን በዓል ለማክበር በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን፣ መንፈሳዊ ነጋዲያን እና የአገር ጎብኚዎች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በእለቱ ቅዱስ ወንጌል ላይ ተንተርሰው አስተንትኖ ማደርጋቸው የሚታወስ ሲሆን በወቅቱ ቅዱስነታቸው አሰተንትኖዋቸውን የጀመሩት የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የማኅበርሰብ ክፍሎች ዘንድ 2019 ዓ.ም መጠናቀቁን እና 2020 ዓ.ም መጀመሩን አውስተው በእዚህ በእለቱ በተጀመረው 2020 ዓ.ም ተስፋችን እና ሰላም የሚለመልምበት በዓል እንዲሆን እንደ ሚመኙ ቅዱስነታቸው ጨምረው ገልጸዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ታዳሚዎች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በታኅሳስ 22/2012 ዓ.ም የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የዓለማችን ማኅበረሰቦች ዘንድ ከተከበረው የ2020 ዓ.ም አዲስ አመት ጋር ተያይዞ የተከበረውን “ማርያም የእግዚኣብሔር እናት” መሆኑዋን በሚዘክረው አመታዊ በዓል ላይ ቅዱስነታቸው በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን፣ መንፈሳዊ ነጋዲያን እና የአገር ጎብኚዎች ያደረጉትን የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ ሙሉ ይዘቱን እንደሚከተለው አሰናድተነዋል እድትከታተሉን ከወዲሁ እንጋብዛለን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ! መልካም አዲስ አመት ይሁንላችሁ!

ትናንት ማታ (ታኅሳስ 21/2012 ዓ.ም) ለተሰጠን ስጦታዎች እና ለተሰጠን ጊዜ ሁሉ እግዚአብሔርን በማመስገን 2019 ዓ.ም መጠናቀቁ ይታወሳል። ዛሬ (ታኅሳስ 22/2012 ዓ.ም) 2020 ዓ.ም እንጀምራለን፣ በተመሳሳይ መልኩም በምስጋና እና በውዳሴ ስሜት እናከብራለን።

በአመቱ የመጀመሪያ ቀን ሥርዓተ አምልኮ ደንብ መሰረት ቅድስት ድንግል ማርያም የእግዚኣብሔር እናት፣ አዳኙን ኢየሱስን የወለደች የናዝሬቷ ድንግል ማርያም በዓል እናከብራለን። ያ ልጅ ለእያንዳንዱ ወንድና ሴት የእግዚአብሔር ታላቅ በረከት ነው። ኢየሱስ ክፋትን ከዓለም አላስወገደም ነግነገር ግን ከሥር መሰረቱ አሸንፎታል። የእርሱ ደኅንነት አስማታዊ የሆነ ደህንነት ሳይሆን ነገር ግን “ታጋሽ” የሆነ ደህንነት ነው፣ ማለትም እሱ የኃጢያትን ኃይል የሚያስወግድ በፍቅር እና በትዕግስት ድል እያደርገ ነው። ምልአት ያለው ፍቅር፣ ፍቅር ታጋሽ ያደርገናል። ብዙ ጊዜ ትዕግሥት እናጣለን ፤ እኔም ቢሆን ይህ ሁኔታ ያጋጥመኛል፣ እኔ ትናንት ላሳየሁት መጥፎ ምሳሌ ይቅርታ እጠይቃለሁ [ምናልባት በታኅሳስ 20/2012 ዓ.ም ላይ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የማኅበረሰብ ክፍሎች ዘንድ 2019 ዓ.ም መጠናቀቁን አስምልክቶ የምስጋና ጸሎት ከተደረገ በኋላ ሕዝቡን ሰላም በማለት ላይ በነበሩበት ወቅት አንዲት ሴት እጃቸውን አጥብቃ ይዛ በመጎተቷ የተነሳ በሰጡት ምላሽ አዝነው ይቅርታ መጠየቃቸው ሊሆን ይችላል)። በዚህ ምክንያት፣ የተወለደው ሕጻን የተኛበትን የክብቶች ማደሪያ ግርግም ትይንት በእምነት ዓይን በመመልከት ከክፉ መንፈስ ነጻ የሆነ ዓለም በግርግም ውስጥ ባለው ሕፃን በክርስቶስ ንጉሣዊ ሥልጣኑ ስር እንደተቀመጠ እናያለን።

ዛሬ የእግዚአብሔር እናት የምትባርከን ለዚህ ነው። እመቤታችን እንዴት ትባርከናለች? ወልድን በማሳየት ትባርከናለች። እሱን በእጆቹ ይዛ አምጥታ ታሳየናለች። እናም እርሱ ይባርከናል። መላውን ቤተክርስቲያን ይባርክ ፣ ዓለምን ሁሉ ይባርክ። በቤተልሔም የነበሩት መልአክት “ሰላምም እርሱ ለሚወዳቸው ሰዎች በምድር ይሁን” (ሉቃ 2፡14) ብለው በደስታ እንደ ዘመሩት ሁሉ የእግዚአብሔር ክብር ለሰው ልጆች ሰላም ነው። በእዚህ ምክንያት የተነሳ ነው ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ጳውሎስ 6ኛ የአመቱ የመጀመሪያ ቀን የሰላም ቀን እንዲሆን ያወጁት፣ ለጸሎት፣ ለግንዛቤ እና ለሰላም ኃላፊነት እንዲሰማን በማሰብ ያወጁት ቀን ነው። ለዚህ  2020 ዓ.ም የዓለም የሰላም ቀን የቀረበው መልእክት እንዲህ ይላል፣ ሰላም የተስፋ መንገድ ነው፣ በውይይት፣ በእርቅ እና ስነ-ምህዳራዊ ልውጥን ከግምት አስገብቶ በመኖር የሚደረግ ጉዞ ነው።

ስለዚህ እይታችንን በእናቱ እና እርሷ በምታሳየን ልጇ ፊት ላይ በማድረግ በእዚህ የዓመቱ መጀመሪያ ቀን ላይ ይባርኩን ዘንድ እንፍቀድላቸው! ማርያም እና ልጇ ሕጻኑ ኢየሱስ እንዲባርኩን እንፍቀድላቸው።

በባርነት ቀንበር ፣ በሥነ ምግባር በባርነት እና በቁሳዊ ባርነት ለተጨቆኑ ኢየሱስ በረከት ነው። በፍቅር ነፃ ያወጣናል። በራስ የመተማመን ስሜቱን አጥቶ በክፉ ጎድና ላይ በመረማመድ ላይ ላሉ ሰዎች ሁሉ ኢየሱስ እንዲ ይላል  “አብ ይወደሃል ፣ አይጥልህም ፣ በማይናወጥ ትዕግስት የእርሱን ዳግም መምጣት ተጠባበቅ የፍትህ መጓደል እና ብዝበዛ ሰለባ ለሆኑ እና መውጫ መንገዱን ላጡ፣ ኢየሱስ የወንድማማችነት ስሜት የሚገለጥበትን በር በመክፈት የእርሱን ፊት እንድንመለከት፣ የእርሱ ልብ እና እጆቹ ወደ ሚገኙበት ስፍራ ይመራናል።

በከባድ ህመም ለሚሰቃዩ፣ ለተረሱ እና ተስፋ ለቆረጡ ሰዎች፣ ኢየሱስ ቅርብ ነው፣ ቁስሎቹን በእርጋታ ይነካል ፣የመጽናናት ዘይትን ያፈሳል እና በጣም የተዘበራረቀውን ሕይወታችንን ለማስተካከል ጥንካሬን እንድናገኝ ያደርገናል። ኢየሱስ በእስር ቤት ውስጥ ለሚገኙ እና ራሳቸውን በእራሳቸው ዝግ አርገው ለሚኖሩ ሰዎች ተስፋቸውን እንደ ገና ያለመልማል።

ውድ ወንድሞች እና እህቶች ፣ ከትዕቢታችን ተላቀን ወደ ታች እንውረድ - ሁላችንም የኩራት ፈተና አለብን - እናም የእግዚአብሄር እናት፣ ትሑት የእግዚአብሔር እናት ከሆነቺው ማርያም በረከትን እንጠይቅ። እየሱስን አሳየችን- እርሱ እንዲባርከን እንፍቀድለት፣ ልባችንን ለእርሱ ፈቃድ እንክፈት። ስለዚህ በእዚህ በምንጀምረው አዲሱ አመት በቃላት ሳይሆን በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ፣ በማስታረቅ እና ለፍጥረታት እንክብካቤ በማድረግ የተስፋ እና የሰላም ጉዞ የምናደርግበት ወቅት ይሆን ዘንድ ያድርግልን።

ይህንን ዘገባ በድምጽ ለመከታተል ከዚህ በታች ያለውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
01 January 2020, 14:45