ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ ወደ ጃፓን ቶኪዮ ሲደርሱ፣ ር. ሊ. ጳ ፍራንችስኮስ ወደ ጃፓን ቶኪዮ ሲደርሱ፣ 

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ወደ ጃፓን በሰላም መድረሳቸው ተነገረ።

ከህዳር 9/2012 ዓ. ም. ጀምሮ በታይላንድ እና በጃፓን 32ኛ ዓለም አቀፍ ሐዋርያዊ ጉብኝታቸውን በማድረግ ላይ የሚገኙት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ትናንት ህዳር 12/2012 ዓ. ም. የታይላንድን ጉብኝት ፈጽመው ወደ ጃፓን መጓዛቸው ታውቋል። ቅዱስነታቸው ዛሬ ህዳር 13/2012 ዓ. ም. በኢትዮጵያ የሰዓት አቆጣጠር ወደ እኩለ ቀን ገደማ ወደ ጃፓን ዋና ከተማ ቶኪዮ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ መድረሳቸውን የቫቲካን ዜና አገልግሎት አስታውቋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ወደ ቶኪዮ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ ሲደርሱ በጃፓን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ፣ በብጹዓን ጳጳሳት እና ቀሳውስት እንዲሁም በስፓኒሽ ቋንቋ “እንኳን ደህና መጡ” የሚል መልእክት የያዙ የካቶሊክ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ደማቅ አቀባበል ያደረጉላቸው መሆኑ ታውቋል። ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በቶኪዮ አውሮፕላን ማረፊያ ውስጥ ባደረጉት አጭር ቆይታ ወቅት ከጃፓን መንግሥት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር የግል ውይይት ማድረጋቸው ታውቋል። ቅዱስነታቸው ቀጥለውም በዋና ከተማዋ ቶኪዮ በሚገኝ የቅድስት መንበር ሐዋርያዊ ጽሕፈት ቤት በተደረገላቸው መስተንግዶ ከአገሪቱ  ካቶሊካዊ ብጹዓን ጋር ተገናኝተው የመጀመሪያ ንግግራቸውን ማድረጋቸው ታውቋል።  

የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የጃፓን ሐዋርያዊ ጉብኝት እስከ ማክሰኞ ህዳር 16/2012 ዓ. ም. ድረስ የሚቆይ መሆኑን የሐዋርያዊ ጉብኝታቸው መርሃ ግብር ያመለክታል።

ይህን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከዚህ ቀጥሎ የሚገኘውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
23 November 2019, 16:47