የር. ሊ. ጳ. ፍራንችስኮስ የሞሪሼስ ሐዋርያዊ ጉብኝት አጫጭር ትዝታዎች።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ሰኞ ጠዋት ጳጉሜ 4/2011 ከማዳጋስካር ዋና ከተማ አንታናናሪቮ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተነስተው ወደ ሞሪሼስ ዋና መዲና ፖርት ሉዊስ ሲደርሱ በአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በክቡር ፕራቪንድ ጁኛውት እና በፖርት ሉዊስ ከተማ ሊቀ ጳጳስ በብጹዕ ካርዲናል ማውሪስ ፒያት ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል። በዋና ከተማዋ ፖርት ሉዊስ በሚገኝ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የሰላም ንግሥት ካቴድራል ውስጥ ወደ 100, 000 ለሚጠጉ ካቶሊካዊ ምዕመናን የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት ስነ ስርዓት ፈጽመዋል። ቀጥለውም እ. አ. አ. በ1970 ዓ. ም. ብጽዕናቸው የታወጀላቸው ሚሲዮናዊ፣ የብጹዕ ጃኮብ ዴዚሬ ቅዱስ አጽም በክብር ወደ ተቀመጠበት ሥፍራ ሄደው ጸሎታቸውን አድርሰዋል። በኋላም ለአገሪቱ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት፣ ለውጭ አገራት ዲፕሎማቶች እና ለሕዝባዊ ተቋማት ተወካዮች ንግግር አድርገውላቸዋል። ማክሰኞ ጠዋት ጳጉሜ 5/2011 ዓ. ም. ወደ ማዳጋስካር ተመልሰው ከአንታናናሪቮ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጉዟቸውን ወደ ሮም አቅንተዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

10 September 2019, 17:13