ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በሮማኒያ የሚያደርጉትን 30ኛውን ሐዋርያዊ ጉብኝት ጀመሩ

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ከግንቦት 23-25/2011 ዓ.ም ድረስ 30ኛውን ሐዋርያዊ ጉብኝት ለማድረግ ወደ ሮማኒያ እንዳቀኑ ቀደም ሲል መገለጻችን የሚታወስ ሲሆን  ቅዱስነታቸው እንደ ተለመደው ማነኛውንም ሐዋርያዊ ጉብኝት ከመጀመራቸው በፊት ሐዋርያዊ ጉብኝት ወደ ሚያደርጉባቸው አገራት ከማቅናታቸው በፊት በቪዲዮ መልእክት እንደ ሚያስተላልፉ የሚታወቅ ሲሆን በዚህም መሰረት ቅዱስነታቸው ወደ ሮማኒያ ለሚያደርጉት ሐዋርያዊ ጉዞ ባስተላለፉት መልእክት እንደ ገለጹት “እኔ ወደ እናንተ የምመጣው ከእናንተ ጋር በመንፈሳዊነት አብሮ ለመጓዝ ነው” ማለታቸውን መዘገባችን ይታወሳል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ለቅዱስነታቸው ከወጣው የጉዞ መረዐ ግብር ለመረዳት እንደ ተቻለው በግንቦት 23/2011 ዓ.ም በሮም ከተማ አቅራቢያ ከሚገኘው የሊዮናርዶ ዳቪንቺ ዓለማቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በኢትዮጲያ የሰዓት አቆጣጠር ከጥዋቱ 03፡10 ላይ ተነስተው የጣሊያንን፣ የክሮሺያን፣ የቦሲኒያን እና የኤርዜጎቪኒያን፣ የሞንቴኔግሮን፣ የሰርቢያን እና የቡልጋሪያን የአየር ክልሎችን አቋርጠው 1,146  ኪሎሜትሮችን በአየር ላይ ተጉዘው 02፡20 ደቂቃ በረራ ካደርጉ በኋላ የሮማኒያ ዋና ከተማ በሆነችው ቡካሬስት ደርሰዋል።

ቅዱስነታቸው በቡካሬስት ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ እንደ ደረሱ የአገሪቷ ርዕሰ ብሔር አቀባበል ያደረጉላቸው ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ ሁለት ባሕላዊ ልብስ የለበሱ ሕጻናት ለቅዱስነታቸው የአበባ ጉንጉን በስጦታ አቅርበዋል። የሮማኒያ የክቡር ዘበኛ የባንድ አባላት ለቅዱስነታቸው አቀባበል ያደረጉላቸው ሲሆን ከእዚያም ባሻገር በሮማኒያ የሚኖሩ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ብጹዕን ጳጳሳት ለቅዱስነታቸው አቀባበል ለማድረግ በአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ መገኘታቸው ተገልጹዋል። 

ይህንን ዘገባ በድምጽ ለመከታተል ከዚህ በታች ያለውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!

Photogallery

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በሮማኒያ የሚያደርጉትን 30ኛውን ሐዋርያዊ ጉብኝት ጀመሩ
31 May 2019, 17:30