ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “ቅዱስ ወንጌል ሁላችንም አገልጋዮች እንሆን ዘንድ ይጋብዘናል” አሉ

የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ በአሁኑ ወቅት የሕማማት ሳምንት እየተከበረ ይገኛል። በእዚህ የሕማማት ሳምንት ውስጥ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ስርዓተ አምልኮ ደንብ መሰረት እኛን ለማዳን እና ከእግዚኣብሔር ጋር እኛን ለማስታረቅ ራሱን መስዋዕት አድርጎ ያቀረበው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተላልፎ መሰጠቱን፣ መንገላታቱን፣ በመስቀል ላይ እንደ ሌባ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ መቀበሩን እና ከሙታን መነሳቱን እነዚህ ሁሉ ነገሮች የተከናወኑባቸው ሦስት ዋና ዋና ቀኖች በተለየ ሁኔታ በታላቅ መንፍሳዊነት ይከበራሉ። ከእነዚህ ቅዱሳን ከሆኑ ቀናት መካከል በቀዳሚነት የሚገኘው የጸሎተ ሐሙስ ቀን ሲሆን በዚህ እለት ኢየሱስ መከራውን ከመቀበሉ በፊት ከደቀ-መዛሙርቱ ጋር የመጨረሻውን ራት ከመብላቱ በፊት የሐዋሪያቱን እግር ያጠበበት፣ እርሱ በምድር ላይ በነበረበት ወቅት የጀመረውን መንፈሳዊ ተልዕኮ እንድያስቀጥሉ በማሰብ ምስጢረ ክህነትን የመሰረተበት፣ የመጨረሻ ራት ከደቀ-መዛሙርቱ ጋር ከተካፈለ በኃላ “ይህንን ለእኔ መታሰቢያ አድርጉ” በማለት ምስጢረ ቅዱስ ቁርባንን የመሰረተበት፣ ብጹዕን ጳጳሳት በእየአገረ ስብከታቸው ከካህናቶቻቸው ጋር መስዋዕተ ቅዳሴን በማሳረግ ምስጢረ ክህነት የተመሰረተበትን ቀን በማስታወስ በጋራ መስዋዕተ ቅዳሴን የሚያሳርጉበት፣ ለምስጢረ ቀንዲል (ሕሙማንን ለመፈወስ የሚያገልግል ቅባ ቅዱስ)፣ ለሚስጢረ ጥምቀት እና ለምስጢረ ክህነት አግልግሎት የሚውሉ ቅባ ቅዱስ በብጽዕን ጳጳሳት የሚባረክበት እለት ተከብሮ ማለፉ ታውቁዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በትልናትናው እለት ማለትም በሚያዝያ 10/2011 ዓ.ም በሮም ከተማ በሚገኝው እና ቬልትሪ በመባል በሚታወቀው ማረሚያ ቤት ተገኝተው በእዚያ ለሚገኙ የሕግ ታራሚዎች መስዋዕተ ቅዳሴ ማሳረጋቸው የታወቀ ሲሆን በወቅቱ ቅዱስነታቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመጨረሻውን ራት ከደቀ-መዛሙርቱ ጋር በበላበት ወቅት የደቀ-መዛሙርቱን እግር ያጠበበት የጸሎተ ሐሙስ ማታ አብነት በመከተል እርሳቸውም የ12 ታራሚዎችን እግር ማጠባቸው የገለጸ ሲሆን “ኢየሱስ እኔ እንዲህ እንዳደረኩላችሁ እናንተም እርስ በእርሳችሁ እንዲሁ አድርጉ” ብሎ መናግሩን ያስታወሱት ቅዱሰንታቸው በልባችን ማዕከል ውስጥ የአገልጋይነት መንፈስ ሊኖር ይገባል፣ “ቅዱስ ወንጌል ሁላችንም አገልጋዮች እንሆን ዘንድ ይጋብዘናል” ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በትላንትናው እለት ማለትም በሚያዝያ 10/2011 ዓ.ም በጸሎተ ሐሙስ ማታ ቬልትሪ በመባል በሚታወቀው ማረሚያ ቤት ተገኝተው መስዋዕተ ቅዳሴ እና የእግር ማጠብ ስነ-ስረዓት መፈጸማቸውን ቀደም ሲል መግለጻችን የሚታወስ ሲሆን ይህ ድርጊት ደግሞ እርሳቸው የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሆነው ከተመረጡ በኋላ በማረሚያ ቤት ተገኝተው ያከናወኑት 5ኛው ስነ-ስረዓት እንደ ነበረ ለመረዳት ተችሉዋል። ይህ በትላንትናው እለት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ የእግር ማጠብ ስነ-ስረዓት እና መስዋዕተ ቅዳሴ ያሳረጉበት የቬትሪ ማረሚያ ቤት እ.አ.አ በ1991 ዓ.ም የተመሰረተ ማረሚያ ቤት ሲሆን በሁኑ ወቅት በእዚህ ማረሚያ ቤት ውስጥ 577 ታራሚዎች የሚገኙ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ 60% የሚሆኑት የጣሊያን ዜግነት የሌላቸው እና ከጣሊያን ውጪ ከሚገኙ አገራት ተወላጅ ታራሚዎች መሆናቸው ተያይዞ የደረሰን ዜና ያመልክታል።

ኢየሱስ የአገልጋይነት መንፈስ የተላበሰ ጌታ ነው!

ቅዱስነታቸው በወቅቱ ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ባሰሙት ስብከት እንደ ገለጹት ኢየሱስ የአገልጋይነትን መንፈስ የተላበሰ ጌታ መሆኑን ገልጸው ምንም እንኳን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የራሱ የሆነ ታላቅ ኃይል የነበረው ቢሆንም በእዚያን ወቅት የአንድ ባሪያ ሰው ተግባር የነበረውን የእግር ማጠብ ስነ-ስረዓት በታላቅ ትህትና ማከናወኑን ቅዱስነታቸው ጨምረው ገልጸዋል።

ኢየሱስ የደቀ-መዛሙርቱን እግር አጠበ። እርሱ ሁሉም ዓይነት ኃይል በእጁ የነበረ፣ እርሱ ጌታ የነበረ፣ አንድ ባሪያ የሆነ ሰው በወቅቱ ያደርገው የነበረውን ተግባር ፈጸመ። ከእዚያም በመቀጠል ለሁሉም ሰዎች “እናንተም በመካከላችሁ እንዲሁ አድርጉ” በማለት ምክሩን ሰጠን፣ ይህም ማለት ደግሞ እያንዳንዳችን ሌሎችን ማገልገል እንዳለብን አሰትማረን። እኛ ወንድማማቾች በመሆናችን የተነሳ ወንድማዊ አገልግሎት ለሌሎች ማበርከት ይገባናል፣ አንዱ ሌላውን ሊጫነው በፍጹም አይገባም፣ ማገልገል ማገልገል ማገልገል የሚለው አስተሳሰብ በውስጣችን ሊሰርጽ ይገባል።

የወንድማማችነት መንፈስ ትሁት እንድንሆን ያደርጋል!

ማገልገል ማለት አንድ የእኛን ርዳታ ለሚሻ ሰው የምናበረክተው አገልግሎት ማለት ነው በማለት ስብከታቸውን የቀጠሉት ቅዱስነታቸው ይህ የአገልግሎት መንፈስ ደግሞ ትሁት በሆነ መንገድ የወንድማማችነት መንፈስ እንዲጠናከር ያደርጋል ብለዋል። እርሳቸውም ቢሆኑ (ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ) ይህንን ቤተ ክርስቲያን ከአንድ ጳጳስ የምትጠብቀውን አገልግሎት ለመፈጸም ዝግጁ መሆናቸውን የገለጹት ቅዱሰንታቸው ይህም ኢየሱስ ያስተማረንን የትህትና መንፈስ እንድንላበስ በማድረግ ለጳጳሱ ለራሱ መልካም የሆነ ተግባር ነው ብለዋል። አንድ ጳጳስ እጅግ በጣም አስፈላጊ አይደለም በማለት በአጽኖት የገለጹት ቅዱስነታቸው ይህንን ሐሳባቸውን ለማጽናት በማሰብ የሚከተለውን ብለዋል. . .

አንድ ጳጳስ አገልጋይ ሊሆን የገባዋል። እያንዳንዳችን የሌሎች አገልጋዮች መሆን አለብን። ይህ ኢየሱስ የሰጠን ደንብ እና በቅዱስ ወንጌል ውስጥ የተጠቀሰ ሕግ ነው፣ የገልግሎት ሕግ፣ በሌሎች ላይ የበላይ ለመሆን ሳይሆን፣ በሌሎች ላይ መጥፎ የሆኑ ተግባራትን ለመፈጸም ሳይሆን፣ ሌሎችን ለማዋረድ ሳይሆን፣ ነገር ግን ሌሎችን ለማገልግለ ሊሆን የግባል።

በልባችን ውስጥ የአገልግሎት መንፈስ ሊኖር ይገባል

ቅዱስነታቸው ስብከታቸውን በቀጠሉበት ወቅት እንደ ገለጹት ኢየሱስ ለደቀ-መዛሙርቱ አንድ ያልተጠበቀ እንግዳ ነገር እንደ ነገራቸው አስታውሰው “የዚህ ዓለም መሪዎች በእናተ ላይ የባልይነትን ለመጎናጸ ይፈልጋሉ” በማለት እንደ ተናገረ ገልጸው ነገር ግን በእነሱ መካከል እንደዚህ መሆን እንደ ማይኖርበት ከእነርሱ መካከል ትልቅ ለመሆን የሚፈልግ ትንሽ መሆን አለበት ብሎ ኢየሱስ ለደቀ-መዛሙርቱ ተናግሮ እንደ ነበረ አስታውሰዋል።

በሕይወት ጎዞ ውስጥ ችግሮች ሊያጋጥሙን እንደ ሚችሉ እሙን ነው፣ እርስ በእርሳችን እንጋጫለን. . ነገር ግን እነዚህ ነገሮች ወዲያውኑ ማለፍ ይኖርባቸዋል፣ አላፊ ነገሮች ሊሆኑም ይገባቸዋል፣ ምክንያቱም በልባችን ውስጥ ሁልጊዜም ቢሆን ሌሎችን የማገልግል መንፈስ ሊኖር ይገባል።

18 April 2019, 11:02