ሁለቱ የደቡብ ሱዳን መሪዎች የሰላም ስምምነት አድርገው፣ ሁለቱ የደቡብ ሱዳን መሪዎች የሰላም ስምምነት አድርገው፣ 

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በደቡብ ሱዳን ሰላም እንዲሰፍን ጥረትን ያደርጋሉ።

በኢትዮጵያ መዲና አዲስ አበባ፣ በኢትዮጵያ፣ በሱዳን፣ በኡጋንዳ እና በኬንያ አደራዳሪነት፣ በሁለቱ መሪዎች ማለትም በሳልቫ ኪር እና በሪክ ማቻር መካከል የተፈረመው የሰላም ስምምነት ከ2005 ዓ. ም. ጀምሮ በአገሪቱ ሲካሄድ የቆየው ጦርነት አክትሞ ሰላምን ለማምጣት የሚያስችል መልካም እርምጃ ነው።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

የቅድስት መንበር ጋዜጣዊ መግለጫ ክፍል ጊዜያዊ አስተባባሪ የሆኑት አቶ አሌሳንድሮ ጂሶቲ ከጋዜጠኞች ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች መልስ በሰጡበት ጊዜ እንዳስረዱት በሚቀጥለው ሳምንት ውስጥ ሁለቱ የደቡብ ሱዳን መሪዎች፣ ፕሬዚደንት ሳልቫ ኪር እና ምክትል ፕሬዚደንት ሪክ ማቻር በቫቲካን ከተማ ተገናኝተው ሱባኤን ለመግባት እቅድ እቅድ እንዳላቸው አስታውቀዋል።

ያለፈው ወር፣ መጋቢት 7 ቀን 2011 ዓ. ም. ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የደቡብ ሱዳን ፕሬዚደንት ሳልቫ ኪርን በቫቲካን ተቀብለው ማነጋገራቸው ይታወሳል። እንደ ቅድስት መንበር ጋዜጣዊ መግለጫ መሠረት፣ ፕሬዚደንት ሳልቫ ኪር ቫቲካንን በጎበኙበት ወቅት እንዳስረዱት፣ በደቡብ ሱዳን ውስጥ በሚገኙ የፖለቲካ ቡድኖች መካከል የተደረሰው የሰላም ስምምነት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ተግባራዊ የሚሆንበትን መንገድ ለመወያየት፣ ጦርነቱ ባስከተለው አደጋ ምክንያት ከመኖሪያቸው ተፈናቅለው የተሰደዱት ወደ መኖሪያ አካባቢያቸው የሚመለሱበትን ሁኔታ ለማመቻቸት እና አገሪቱ ሁለ ገብ ማሕበራዊ እድገት የምታመጣበትን መንገድ ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ጋር ለመወያየት መሆኑን ጋዜጣዊ መግለጫ ክፍሉ አስታውቋል።

የደ. ሱዳን ካቶሊካዊ ብጹዓን ጳጳሳት “የሰላም ስምምነት ውሉ መልካም እርምጃ ቢሆንም ጦርነቱ አላበቃም፣

የደቡብ ሱዳን ብጹዓን ጳጳሳት ያለፈው ጥር ወር 2011 ዓ. ም. በዋና ከተማ ጁባ ባካሄዱት ጠቅላላ ጉባኤ ማጠቃለያ ላይ ይፋ ባደረጉት መልዕክታቸው እንዳስገነዘቡት፣ በፖለቲካ ተቀናቃኞች መካከል የሰላም ስምምነት ውል ቢፈረምም በአገሪቱ የተነሳው አመጽ እና ጦርነት እንዳላከተመ ገልጸዋል። ብጹዓን ጳጳሳቱ በመልዕክታቸው እንደገለጹት በኢትዮጵያ መዲና አዲስ አበባ፣ በኢትዮጵያ፣ በሱዳን፣ በኡጋንዳ እና በኬንያ አደራዳሪነት፣ በሁለቱ መሪዎች ማለትም በሳልቫ ኪር እና በሪክ ማቻር መካከል የተፈረመው የሰላም ስምምነት ከ2005 ዓ. ም. ጀምሮ በአገሪቱ ሲካሄድ የቆየው ጦርነት አክትሞ ሰላምን ለማምጣት የሚያስችል መልካም እርምጃ ነው ብለው ወደ ስምምነቱ ለመድረስ ግን 15 ወራት ማስቆጠሩን አስታውቀዋል። ብጹዓን ጳጳሳቱ በመልዕክታቸው እንደገለጹት ከስምምነቱ በኋላም ቢሆን የግጭቶች አለመብረድ የግጭቶቹ ትክክለኛ መንሴዎች ላይ ግልጽ ውይይት አለመደረጉን ያመላክታል ብለዋል። በስልጣን ክፍፍል ላይ ብቻ ትኩረት ያደረገ ውይይት ወይም ስምምነት የአገሪቷን አጠቃላይ ሰላም እና ደህንነት አላገናዘበም ብለዋል።

የሰብዓዊ መብቶች መጣስ ቀጥሏል።

የደቡብ ሱዳን ካቶሊካዊ ብጹዓን ጳጳሳት በማከልም የተደረሰው ስምምነት ተግባራዊነት እንደዘገየ ገልጸው ተቃዋሚ ወገኖች በተደረገው ስምምነት መሠረት ተኩስ ማቆም ሲገባቸው ነገር ግን ጦርነትን እና አመጽን በማስፋፋት፣ የጾታ ጥቃቶችን በማድረስ፣ ቅሚያን፣ የመሬት ዝርፊያን እና የሕዝብ ንብረት ዘረፋን እንዳባባሰው ገልጸው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እየተፈጸመ መሆኑን ገልጸዋል። ካቶሊካዊ ብጹዓን ጳጳሳት በመልዕክታቸው፣ ስለ ሰላም በስፋት ቢወራም ያስገኘው ውጤት እምብዛም በውል አይታይም ብለው ለሁሉም የፖለቲካ ተቀናቃኞች ባቀረቡት ጥሪ በኩል፣ ተቀናቃኝ የፖለቲካ ቡድኖች እውነተኛ ሰላምን ማምጣት የሚፈልጉ ከሆነ የበኩላቸውን አስተዋጽዖ እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል።

ይህን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከዚህ ቀጥሎ የሚገኘውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
04 April 2019, 17:22