ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “ሕግን በማክበር እና በመንፈስ ቅዱስ በመመራት ጌታን ማገልገል ያስፈልጋል”

የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ ጥር 25/2011 ዓ.ም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሕጻንነቱ በወላጆቹ አማካይነት ወደ ቤተ መቅደስ የተወሰደበት ቀን የሚዘከርበት ዓመታዊ በዓል በታላቅ ድምቀት ተከብሮ ማለፉ ታውቁዋል። ከዚህ በዓል ጋር መሳ ለመሳ በሆነ መልኩ ጌታ ለሚያቀርብላቸው መንፈሳዊ ጥሪ ልዩ በሆነ ሁኔታ ራሳቸውን አሳልፈው በመስጠት በተላያየ መንገድ እግዚኣብሔርን በማገልግል ላይ የሚገኙ ወንድ እና ሴት ገዳማዊያን ገዳማዊያት 23ኛው ዓለም  አቀፍ በዓል ተከብሮ ማለፉ የሚታወስ ሲሆን ይህ በዓል በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በእርሳቸው መሪነት ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ተከብሮ ማለፉን ለመረዳት የተቻለ ሲሆን ቅዱስነታቸው በወቅቱ ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ባሰሙት ስብከት እንደ ገለጹት “ሕግን በማክበር እና በመንፈስ ቅዱስ በመመራት ጌታን ማገልገል ያስፈልጋል” ማለታቸውን ለመረዳት ተችሉዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በእለቱ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አባዚሊካ ያደርጉትን የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው አዘጋጅተነዋል ተከታተሉን።

የዛሬው ቀን ስርዓተ አምልኮ ኢየሱስ ሕዝቡን ለመገናኘት መሄዱን ያሳየናል። የግንኙነት በዓል ነው፡ አዲስ የተወለደው ሕጻን ከቤተ መቅደስ ባሕል ጋር ሲተዋወቅ እናያለን፣ የተገባው ቃል ኪዳን እውን ሲሆን እናያለን፣ ወጣት የነበሩ ማርያም እና ዮሴፍ እድሜ ጠገቦቹን ስምዖንን እና ሐናን ሲገናኙ እንመለከታለን። ስለዚህ ሁሉም ነገሮች በኢየሱስ መምጣት የተነሳ ሲገናኙ እናያለን።

ይህ ለእኛ ምን ማለት ነው? ከሁሉም በላይ ደግሞ እኛ እኛን ለመገናኘት የመጣውን ኢየሱስን ለመቀበል እንደ ተጠራን ያመለክታል። እሱን ለመገናኘት፣ ሕይወት ሰጪ የሆነውን አምላክ በዕየለቱ በህይወታችን ውስጥ መገናኘት መቻል ይኖርብናል፣ ዛሬ እና ከዛሬ በስቲያ ባሉ ቀናት ውስጥ ሳይሆን ነገር ግን በእየቀኑ ኢየሱስን መከተል ይኖርብናል። ኢየሱስን ለመከተል የሚደረጉ ውሳኔዎችን ማድረግ ማለት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እርሱን ለመከተል የሚደርጉ ቁርጥ ውሳኔዎችን ማድረግ ብቻ ማለት አይደለም፣ ነገር ግን በእየለቱ የምናደርገው ምርጫ ሊሆን ይገባዋል። እናም ጌታን የምናገኘው በተዘዋዋሪ ሳይሆን ነገር ግን በቀጥታ በህይወታችን ውስጥ እናገኘዋለን። አለበለዚያ ግን ኢየሱስ ያለፈው ጊዜ አስደሳች ትዝታ ብቻ ሆኖ ይቀራል ማለት ነው። ኢየሱስን የሕይወታችን ጌታ አድርገን ስንቀበለው፣ ኢየሱስን የሕይወታችን ማዕከል እና የሁሉም ነገራችን የልብ ምት አድርገን ስንቀበለው፣ እርሱ ሕያው እና አዲስ በሆነ መልኩ በእኛ ውስጥ ይኖራል። በቤተመቅደስ ውስጥ የተከናወነው ነገር ሁሉ በእኛም ላይ እንዲሁ ይደርስብናል፣ በእርሱ ዙሪያ ሁሉም ነገሮች የተገናኙ ናቸው፣ ሕይወትም እርስ በእርሱ በሚስማማ መልኩ ኅብረት ይፈጥራል። ከኢየሱስ ጋር በመሆናችን ጉዞዎቻችንን እንድንቀጥል እና ጠንክረን እንድንቆም ያደርገናል። ከጌታ ጋር መገናኘት ደግሞ የእዚሁ ሁሉ ምንጭ ነው። በዚህም ምክንያት ወደ ስር መሰረታችን መመለስ ባጣም አስፈላጊ ነው፣ ከእርሱ ጋር ለመገናኘት ወሳኝ የሆነ ጊዜ በአእምሮኋችን ውስጥ ማሰላሰል ይገባናል፣ መጀመሪያ የነበረንን ፍቅራችንን ማደስ፣ ምንአልባትም እኛ ከጌታ ጋር የነበረንን የፍቅር ታሪክ በድጋሚ በመፈጸም ሊገለጽ ይችላል። ይህ መንፈሳዊ የሆነ ሕይወት ለሚኖሩ ሰዎች መልካም ነገር ነው፣ ይህንንም ማደርጋችን እንዲያው ለይስሙላ ጊዜ ማሳለፊያ አድረግን የምንጠቀምበት ነገር ሳይሆን ከኢየሱስ ጋር በድጋሚ እንድንገናኝ እድሉን የሚከፍትልን አጋጣሚ በመሆኑ የተነሳ ነው። ከጌታ ጋር የነበረንን የመጀመሪያውን ግንኙነት በአእምሯችን ስናስታውስ ይህ በእኛ እና በእግዚአብሔር መካከል ብቻ የተፈጠረ ግላዊ ነገር አለመሆኑን እንረዳለን። እንዲ አይደለም! በብዙ ወንድሞች እና እህቶች ውስጥ፣ በተወሰኑ ጊዜያት እና ቦታዎች፣ አማኝ ከሆኑ ሰዎች አውድ ጋር የሚገናኝ እና አብሮ የሚሄድ ነገር ነው። ይህንን በተመለከተ ቅዱስ ወንጌል ብዙ ነገሮችን የሚናገር ሲሆን ሁሉም ግንኙነቶች የተከሰቱት በእግዚኣብሔር ሕዝብ መካከል ወይም ውስጥ፣ በተግባራዊ እና ተጨባጭ በሆነ ታሪኩ ውስጥ፣ በሕይወት ወጎቻቸው ውስጥ፣ በቤተ መቅደስ ውስጥ፣ በሕግጋት ውስጥ፣ በትንቢት አውድ ውስጥ፣ በወጣቶች እና በአረጋዊያን ውስጥ (ሉቃ 2፡25-28,38) እንዴት እንደሚከናወን ቅዱስ ወንጌል ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል። በመንፈሳዊ ሕይወት ውስጥም ቢሆን እንዲሁ ነው የሚከሰተው፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥም በዚሁ መልኩ ነው በቅሎ የሚያብበው፣ ሕብረት ከሌለ ግን ይጠወልጋል። ወጣቱና አረጋውያኑ አብረው ሲጓዙ፣ ወጣቱ ስር መሰረቱን ፈልጎ በድጋሚ ሲያገኝ እና  አረጋውያን እነዚህን ፍሬዎች በደስታ ሲቀበሉ ፍሬ ያፈራል። ብቻችንን ስንጓዝ፣ ባለፈው ጊዜ ላይ ተጣብቀን ስንኖር ወይም ለመኖር ስንሞክር ወይም ወደ ፊት ዘለን በመሄድ ሕልውናችንን ልናስጠብቅ ስንሞክር መንፈሳዊ ሕይወታችን እዚያ ደርቆ ይቀራል። ዛሬ በሚከበርው የግንኙነት የበዓል ቀን ውስጥ፣ ሕያው የሆነ አምላካችንን መልሰን በአዲስ መልክ መገናኘት እንችል ዘንድ ጸጋውን እንዲሰጠን እርሱን በመጠየቅ በተጨማሪም ዛሬ የተቀበልናቸውን ጸጋዎች በሚገባ መጠቀም እንችል ዘንድ ጸጋውን እንዲሰጠን እርሱን እንጠይቃለን።

በተጨማሪም ቅዱስ ወንጌል እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር የሚገናኝበት መነሻ ነጥብ እና እንዲሁም መድረሻ ግብ እንዳለው ይናገራል። ይህም በቤተመቅደስ በተደረገው ጥሪ ይጀምርና በመቀጠል ደግሞ በእዚያው በቤተመቅደስ ውስጥ በሚከሰተው ራዕይ ላይ ይደርሳል። ይህም ጥሪ ሁለት ዓይነት ገጽታ እንዳለው ያሳያል። የመጀምሪያው “ሕግን መስረት ያደርገ ነው” (ሉቃስ 2፡22)። ይህም ማርያም እና ዮሴፍ በሕግ የተደነገገውን ትዕዛዝ ለመፈጸም ወደ ቤተ መቅደስ መሄድ እንዳለባቸው የሚጠቁም ጥሪ ነው። ይህ የቅዱስ ወንጌል ክፍል በሕግ እንደ ተደነገገ” በማለት ስለ ጉዳዮ አራት ጊዜ አጽንዖት በመስጠት ይናገራል (ሉቃ. 2፡22,23,24,27)። ይህ አስገዳጅ የነበረ ሕግ አይደለም፣ በዚህም የተነሳ የኢየሱስ ወላጆች ይህንን የመፈጸም ተጫማሪ ግዴታ አልነበረባቸውም፣ ተግባራዊ ለማድረግም አይገደዱም። የሄዱበት ዋነኛው ምክንያት ለእግዚኣብሔር ጥሪ ምላሽ ለመስጠት ነው። ሁለትኛው ዓይነት ጥሪ ደግሞ መንፈስ ቅዱስ የሚያቀርብልን ዓይነት ጥሪ ነው”። ይህም ለስምዖን እና ለሐና የደርሰው ዓይነት ጥሪ ነው። ይህም ደግሞ ጠንካራ የሆነ አጽንዖት ተሰጥቶት  ነበር፣ ስምዖንን በተመለከተ ሶስት ጊዜ (ሉቃ. 2፡25,26,27) በአጽንዖት ተገልጾ በመንፈስ ቅዱስ አነሳሽነት ወደ እግዚአብሔር በቀረበችው በነቢዪቱ በሐና የምስጋና ውዳሴ ይጠናቀቃል (ሉቃ. 2፡38)። በህግ የተጠሩት ሁለት ወጣቶች ወደ ቤተመቅደስ ለመሄድ ሲሯሯጡ፣ ሁለት አረጋውያን ደግሞ በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ሲንቀሳቀሱ እናያለን። እነዚህ በሕግ እና በመንፈስ ቅዱስ መጠራት የሚሉት ሁለት ገጽታዎች ለእኛ መንፈሳዊ ሕይወት እየኖርን ለምንገኝ ሰዎች ምን ማለት ይሆን? ያም ማለት ደግሞ እኛ ሁላችንም ሁለት ዓይነት ገጽታ ያለው ተዐዝዞ ጠብቀን እንድንኖር ተጠርተና ማለት ነው፣ በቅድሚያ ለሕግ ታዝዥ እንድንሆን--ይህም ሕይወታችንን በስርዓት እንድንመራ ያደርገናል - ለመንፈስ ቅዱስ ታዛዥ መሆን ደግሞ- በሕይወታችን አዲስ ነገር እንዲከሰት ያደርጋል። በዚህም የተነሳ ከጌታ ከእግዚአብሔር ጋር የምናደርገው ግንኙነት በአዲስ መልክ ይወለዳል ማለት ነው፣ ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ እግዚኣብሔርን ይገልጣል፣ ያንን መንፈስ ቅዱስ ለመቀበል ግን በየቀኑ በጽናት መጠባበቅ ያስፈልጋል። ምንም እንኳን መልካም የሆነ ስነ-ምግባር ወይም መንፈሳዊነት ቢኖረንም ያለ ተዐዝዞ ግን ፍሬያማ ሊሆን አይችልም። ይህ ማለት ሕግን ማክበር አስፈላጊ ነው ማለት ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ምርጥ የሚባሉ ሕጎች ቢኖሩም እንኳን የመንፈስ ቅዱስ መሪነት የማይታከልበት ከሆነ ግን ዋጋ የለውም ወይም በቂ አይደለም፣ ሕግ እና መንፈስ ቅዱስ አብረው የሚሄዱ፣ ሊነጣጠሉ የማይገባቸው እውነታዎች ናቸው።

በኢየሱስ ሕይወት የመጀመሪያዎቹ ቀኖች ውስጥ ዛሬ በዚህ ቤተመቅደስ ውስጥ የተመለከትናቸው እነዚህን ጥሪዎች በተሻለ ሁኔታ ለመረዳት፣ ኢየሱስ በዚህ ምድር ላይ የነበረውን ተልዕኮ እና አገልግሎቱን በይፋ በጀመረበት ወቅት በቃና ዘገሊላ ሰርጋ ላይ ውኃን ወደ ወይን ጠጅ የቀየረበትን አጋጣሚ ማስታወስ ያስፈልጋል። እዚያም ቢሆን የተዐዝዞ ጥሪ እንደ ነበረ እንገነዘባለን፣ ማርያምም እርሱ የሚላችሁን አድርጉ” (ዮሐ. 2፡5) በማለት ተናግራ ነበር። የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ። ኢየሱስ አንድ ለየት ያለ ነገር ይጠይቀናል፣ እርሱ በድንገት ተነስቶ አንድ አዲስ ነገር አያደርግም፣ ውሃውን ወደ ወይን ጠጅ የቀየረው እንዲያው ከባዶ ነገር ተነስቶ አይደለም፣ እርሱ ተጨባጭ እና አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን ይጠይቀናል። በሕግ በታዘዘው መሰረት የመንጻት ስነ-ስርዓት የሚካሄድባቸው ውሃ የሚሞላባቸው ስድስት የድንጋይ ጋኖችን ውሃ እንዲሞሉባቸው ጠየቃቸው። ይህም ሰለ ሕግ ያስታውሰናል። ይህም ማለት 600 ሊትር የሚሆን ውሃ ከጉድጓድ በማውጣት ጋኖቹን መሙላት ማለት ነው፣ ይህም ጊዜ እና ጉልበትን ይጠይቅ ነበር፣ የሚፈለገው ውሃ ሳይሆን የወይን ጠጅ በመሆኑ የተነሳ ይህንን ማድረጉ ደግሞ ትርጉም የለሽ ነበር። ሆንም ግን ከእነዚያ እስከ “አንገታቸው ድረስ ውሃ ከተሞሉ” (ዮሐ. 2፡7) ጋኖች ውስጥ ኢየሱስ አዲስ የወይን ጠጅ እንዲቀዳ አደረገ። ለእኛም የሚሆነው እንዲሁ ነው፣ እግዚአብሔርን በታማኝነት እና ተጨባጭ በሆኑ ነገሮች እንድንገናኘው ይጠራናል፣ እነዚህም ተጨባጭ የሚባሉ ነገሮች እለታዊ ጸሎት፣ መስዋዕተ ቅዳሴን መካፈል፣ ምስጢረ ንስሐን ማዘውተር፣ እውነተኛ የሆነ የፍቅር ተግባር መፈጸም፣ በእየለቱ የእግዚኣብሔርን ቃል ማንበብ። ለአለቆቻችንን ተጨባጭ በሆነ መልኩ መታዘዝ እና የመንፈሳዊ ሕይወት ሕግ ጋትን ማክበር። ይህንን ህግ በፍቅር ካከበርን ልክ በቤተ-መቅደስ እና በቃና እንደነበረው ክስተት፣ መንፈስ ቅዱስ በእኛ ላይ በመውረድ ያልተጠበቀውን የእግዚአብሔር ጸጋ ይሰጠናል። ስለዚህ የዕለት ተዕለት ውኃችን ወደ አዲስ ሕይወት ወይን ጠጅ ይለወጣል፣ የተወሳሰበ የሚመስለውን ሕይወታችንን በነጻነት መንፈስ ይሞላል።

ከእርሱ ጥሪ የተወለደ ሰው በራዕይ ያድጋል። ስምዖንም ዓይኖቼ የእግዚኣብሔርን መዳን አይተዋልና” (ሉቃ.2፡30) በማለት ተናግሮ ነበር። እርሱ ልጁን ካየው በኋላ የእራሱን ደህንነት ይመለከታል። እርሱ ተመልክቶት የነበረው ተዐምር የሚሰራውን መስሕ ሳይሆን ሕጻኑን ኢየሱስ ነበር። እርሱ በጣም ልዩ የሆነ ነገር አልተመለከተም ነበር፣ ነገር ግን ሕጻኑን ኢየሱስ በጣም ዝቅተኝ የተባለ የሚስኪኖች መስዋዕት ተደርጎ ይቆጠር የነበሩትን ሁለት ርግቦች ወደ ቤተመቅደስ ይዘው ከመመጡ ከወላጆቹ ጋር ነበር የተመለከተው። ስምዖን የእግዚአብሔርን ትህትና ተመልክቶ እርሱ በደስታ ይቀበላል። ስምዖን ሌላ ምንም ነገር አልፈለገም ነበር፣ ተጨማሪ ነገር እየጠየቀ ወይም አይፈለገም አልነበረም፣ ልጁን ለማየት እና እርሱ ካቀፈው በኋላ ባሪያህን በሰላም አሰናብተው” (ሉቃ. 2፡29) ለማለት ብቻ ነበር የፈልገው። ለእርሱ እግዚኣብሔርን ማየት ብቻ በቂ ነበር። በእግዚያብሔር ውስጥ የሕይወቱን ዋነኛ ትርጉም ያገኛል። ይህ በእውነታችን እና በእጆቻችን ውስጥ ጌታን በምናከብርበት፣ ማንንም ሳናገል የተቀደሰ ሕይወት ለመኖር የተሰጠን የሕይወት ትንቢታዊ ራእይ ነው። እርሱ የእኛ ሕይወት ነው፣ እርሱ ተስፋችን ነው፣ እርሱ የእኛ የወደፊት ጊዜ ነው።

የተቀደሰ ሕይወት መኖር ማለት ለሕልውናችን ብቻ የሚበጁንን ነገሮች ማድረግ ማለት ሳይሆን አዲስ የሆነ ሕይወት መኖር ማለት ነው። ከጌታ ጋር በቤተ መቅደስ ውስጥ መገናኘት ማለት ነው። ይህም ዕለት በዕለት ኑሮዋችን በታማኝነት በመታዘዝ መኖር እና መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠንን ያልተጠበቁ ድንገተኛ ስጦታዎችን ለመቀበል መዘጋጀት ማለት ነው።  የሁላችንም ራዕይ የሆነውን የደስታችን ምንጭ የሆነውን ኢየሱስን ለመገናኘት መትጋት ማለት ነው።

02 February 2019, 08:57