ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሻ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሻ  

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ “እግዚአብሔርን ‘አባት’ ብሎ ከመጥራት የበለጠ ልብ የሚነካ ስሜት የለም”

"አባ" የሚለው አገላለጽ በጣም አስተማማኝ እና በተለመደ መልኩ በተደጋጋሚ የምንጠቀምበት በመሆኑ የተነሳ ለክርስቲያኖች በጣም አስፈላጊ የሆነ ቃል ነው።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራቸስኮስ ዘወትር ረቡዕ እለት በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ወይም በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሻ ለሚሰበሰቡ ምዕመናን፣ መንፈሳዊ ነጋዲያን እና የሀገር ጎብኝዎች በተለያዩ አርእስቶች ላይ ተመርኩዘው የጠቅላላ የትምሕርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ ይታወቃል። በዚህ መሰረት በኅዳር 26/2011 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ ያደርጉት የጠቅላላ የተምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ “አባታችን ሆይ” በሚለው ጸሎት ዙሪያ ላይ መሰረቱን ያደርገ የክፍል አንድ አስተምህሮ እንደ ነበረ መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን “ኢየሱስ ጸሎት መጸለይ እንዲይስተምረን ልንጠይቀው ይገባል” ማለታቸውን መዘገባችን ይታወሳል።
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
በታኅሳስ 03/2011 ዓ.ም አሁንም “አባታችን ሆይ” በሚለው ጸሎት ዙርያ ላይ ባደርጉት የክፍል ሁለት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ “አባታችን ሆይ” የሚለውን ጸሎት “በእግዚኣብሔር በመተማመን ልንጸልየው የሚገባን ጸሎት ነው” ማለታቸውንም መዘገባችን ይታወሳል። በታኅሳስ 24/2011 ዓ.ም አሁንም “አባታችን ሆይ!” በሚለው ጸሎት ዙርያ ላይ ባደርጉት የክፍል ሦስት የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ “ሳትለምነው በፊት ምን እንደ ሚያስፈልግህ በሚያውቀው አባትህ ፊት ሆነህ ጸልይ” (ማቴ. 6፡6) የእኛ አምላክ የሆነው እግዚኣብሔር እርሱ ከእኛ ምንም አይፈልግም፣ ነገር ግን እርሱ ከእኛ የሚፈልገው አንድ ነገር ቢኖር የእርሱ በጣም ተወዳጅ ልጆቹ የሆንን እኛ በጸሎት ሁልጊዜ ከእርሱ ጋር ለመገናኘት የሚያስችለንን የመገናኛ መስመር ሁልጊዜ ክፍት እንድናደርግ ብቻ ነው የሚጠይቀን” ማለታቸውን መዘገባችን ይታወሳል። በጥር 1/2011 ዓ.ም አሁንም “አባታችን ሆይ” በሚለው ጸሎት ዙርያ ባደርጉት የክፍል አራት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ቅዱስነታቸው እንደ ገለጹት “ማነኛውም ዓይነት ጸሎት ወደ እግዚ/ር ዘንድ ሳይደርስ እንዲሁ በከንቱ አይቀርም! እርሱ እግዚኣብሔር አባት በመሆኑ የተነሳ በመከራ ውስጥ ሆነው እርሱን የሚለምኑትን ልጆቹን በፍጹም አይረሳም” ማለታቸውን ባልፈው ሳምንት መዘገባችን ይታወሳል።
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ከዚህ ቀደም “አባታችን ሆይ” በሚለው ጸሎት ዙሪያ በተከታታይ ያደረጉትን የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ይህን ያህል ካስታወስናችሁ በዛሬው እለት ማለትም በጥር 08/2011 ዓ.ም “አባታችን ሆይ!” በሚለው ጸሎት ዙሪያ ባደረጉት የክፍል አምስት የጠቅላላ የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ቅዱስ ሐዋርያዊ ጳውሎስ ወደ ሮም ሰዎች በጻፈው መልእክቱ (8፡14-16) ላይ በተጠቀሰው እና “አባ አባት ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁም” (ሮም. 8፡15) በሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ላይ መሰረቱን ያደርገ እንደ ነበረ ለመረዳት የተቻለ ሲሆን ““አባ" ማለት እግዚአብሔርን "አባት" ብሎ ከመጥራት የበለጠ ልብ የሚነካ ስሜት እንደ ሌለ ያሳየናል” ማለታቸውን ለመረዳት ተችሉዋል።

በእለቱ የተነበበው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል

“በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና። አባ አባት ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና።
የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ያ መንፈስ ራሱ ከመንፈሳችን ጋር ይመሰክራል” (ሮም. 8፡14-16)

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ተከታታዮች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ “አባታችን ሆይ” በሚለው ጸሎት ዙሪያ በጥር 08/2011 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ ያደርጉትን የጠቅላላ አስተምህሮ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው እናቀርብላችኋለን እንድትከታተሉን ከወዲሁ እንጋብዛለን።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደ ምን አረፈዳችሁ!
ከዚህ ቀደም “አባታችን ሆይ” በሚለው ጸሎት ዙሪያ ጀምረነው የነበረውን የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ በመቀጠል ዛሬ ደግሞ በአዲስ ኪዳን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ ይህ ጸሎት “አባ አባት” ወደ ሚለው ወደ አንድ በጣም አስፈላጊ ወደ ሆነ ቃል የሚሻገር እንደ ሆነ እንረዳለን።
ቅዱስ ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ሮም ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ውስጥ የተጠቀሰውን “አባ አባት” ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁም” (ሮም. 8፡15) በማለት የተናገረውን ቃል ሰምተናል። ቅዱስ ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ገላትያ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ደግሞ “ልጆችም ስለ ሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮኽ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ” (ገላትያ 4፡6) በማለት አክሎ ይናገራል። ይህ ሁለት ጊዜ በተመሳሳይ መልኩ የቀረበ መልእክት በአዲስ መልክ በቅዱስ ወንጌል ውስጥ ተጠቃሎ ይገኛል። ኢየሱስ ክርስቶስን ካወቀ በኋላ የእርሱን ስብከት ሰምቶ ካዳመጠ በኋላ አንድ ክርስቲያን እግዚአብሔርን እንደ አምባገነን ሰው አይፈራም፣ ምንም ዓይነት ፍራቻ ሊኖረው አይችልም፣ ነገር ግን በእርሱ ላይ እምነት እንደሚጥልበት ስለሚሰማው ፈጣሪውን "አባት" ብሎ ሊጠራው ይችላል። ይህ "አባ" የሚለው አገላለጽ በጣም አስተማማኝ እና በተለመደ መልኩ በተደጋጋሚ የምንጠቀምበት በመሆኑ የተነሳ ለክርስቲያኖች በጣም አስፈላጊ የሆነ ቃል ነው።
በአዲስ ኪዳን ውስጥ በህብራይስጥ ቋንቋ የተገለጹ አባባሎች ወደ ግሪክ የመተርጎማቸው እንድል እምብዛም የተለመደ አይደለም። በዚህ የህብራይስጥ ቋንቋ አጠቃቀም የተነሳ የኢየሱስ የራሱ ድምጽ “ተቀረጾ” መቀመጡን መገመት እንችላለን። በዚህም የተነሳ “አባታችን ሆይ" በሚለው ጸሎት መጀመሪያ ቃል ውስጥ ወዲያውኑ የክርስቲያን ጸልት በአዲስ መልክ እናገኛለን።
የአባትን ምስል ምስጢራዊነት መጠቀሙ ብቻ አይደለም - ከእግዚአብሔር ምሥጢር ጋር የተገናኘ ነው፡ ይልቁንም መላው ዓለም በኢየሱስ ልቡ ውስጥ ይፈወሳል ማለት ነው። ይህንን በተግባር ላይ የምናውለው ከሆነ ደግሞ "አባታችን ሆይ" የሚለውን ጸሎት በእውነት መጸለይ እንችላለን ማለት ነው። “አባ" ማለት እግዚአብሔርን "አባት" ብሎ ከመጥራት የበለጠ ልብ የሚነካ ስሜት እንደ ሌለ ያሳየናል። ለዚህ ነው እንግዲህ አንድ ሰው ቀደም ሲል የነበረውን ቋንቋ ተጠቅሞ “አባቴ” ወይም ደግሞ “አብዬ” በማለት ይህንን ቃል የተረጎመው በዚሁ ምክንያት ነው። እንደ እውነቱ ከሆነ እነዚህ አገላለጾች ልጆች ከመሆናችን አኳያ ፍቅርን የሚገልጹ፣ ሞቅ ያለ ስሜት እንዲኖረን የሚያደርጉ፣ ዘላለማዊ የሆነ ፍቅር እና ርኅራኄ ለልጁ የሚያሳይ በአባቱ እቅፍ ውስጥ እንዳለ አንድ ሕጻን ልጅ ሆነን እንዲሰማን እንደ ሚያደርገን ማሰብ ይቻላል።
ነገር ግን በዚህ ረገድ ይህንን ቃል በተሻለ መልኩ ግልጽ በሆነ ሁኔታ የሚተረጎመው በቅዱስ ወንጌል ውስጥ ነው። አንድ ሰው ጠፍቶ የተገኘውን ልጅ ታሪክ በሚገለጸው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ውስጥ በዋነኛነት የተገለጸውን አባት ርኅራኄ የሚገልጸውን ታሪክ ካነበበ በኋላ (ሉቃስ 15፡11-32) “አባታችን ሆይ” የሚለውን ጸሎት ቢጸልይ የጸሎቱን እውነተኛ ትርጉም በምልኣት ሊረዳ ይችላል። ረዘም ላለ ጊዜ በትዕግሥት ሲጠባበቀው የነበረውን የአባቱ እቅፍ ካየው፣ እርሱ የተናገራቸውን ጎጂ የሆኑ ቃላትን በፍጹም የማያስታውሰውን አባቱን ያገኘውን፣ አሁን ደግሞ እንዲያው በቀላሉ ልጁ ምን ያህል እንደ ናፈቀው እንዲረዳ ያደረገውን አባት የተገናኘውን ጠፍቶ የተገኘው ልጅ ይህንን “አባታችን ሆይ” የሚለውን ጸሎት እንደ ጸለየ አድርገን እንውሰድ። ከዚያም እነዚህ ቃላት እንዴት ሕይወት ሰጪ የሆኑ ቃላት እንደ ሆኑ እንረዳለን፣ ጥንካሬም ይሰጡናል። እግዚአብሔር የሚታውቀው በፍቅሩ ብቻ ነው ወይ? በቀል በአንተ ውስጥ ቦታ አለው ወይ? የፍትህ ጥያቄ በአንተ ውስጥ ይነሳል ወይ? ክብርህን የሚነካ ነገር በመፈጸማችን የተነሳ በአንተ ውስጥ ንዴት ቦታ አለው ወይ? ብለን ራሳችንን ልንጠይቅ ይገባል።
በዚያ ምሳሌ ውስጥ የተጠቀሰው አባት የአንድ እናት ነፍስን የሚያስታውሰን አንድ ነገር አለው። ከሁሉም በላይ ደግሞ ልጆቻቸውን ይቅር ማለት የሚችሉ እናቶች እንደ ሆኑ እንረዳለን፣ ለልጆቻቸው ያላቸውን ርኅራኄ ላለማቋረጥ የሚተጉ፣ ለልጆቻቸው መልካም ነገሮችን ሁሉ በቀጣይነት የሚመኙ፣ ምንም እንኳ ልጆቻቸው በተለያዩ ጥፋቶች ምክንያት እነዚህ ነገሮች የሚገቧቸው ባይሆኑም እንኳን እነዚህ መልካም ነገሮች በቀጣይነት የሚፈጽሙ እናቶች ናቸው።
የክርስትናን ጸሎት ለማዳበር ይህንን “አባ” የሚለውን ቃል በመጠቀም ማሳደግ ይቻላል። ቅዱስ ሐዋርያው ጳውሎስ በጻፋቸው መልእክቶች ውስጥ ይህንን ተመሳሳይ መንገድ ተከትሎ የሄደውም በዚሁ ምክንያት ነው፣ ምክንያቱም ይህ ከኢየሱስ የተማረው መንገድ ስለሆነ ነው፣ በዚህ ጥሪ ውስጥ የቀሩትን ነገሮች ሁሉ ቀልብ የሚስብ ኃይል በመኖሩ የተነሳ ነው።
ምንም እንኳን አንተ ባትፈልገውም፣ እግዚአብሔር ግን አንተን ይፈልግሃል። እግዚአብሔርን ብትረሳውም እርሱ ግን አንተን መውደዱን ይቀጥላል። ምንም እንኳን በአንተ ውስጥ ያሉ ችሎታዎች ሁሉ በከንቱ እንዳባከኑ አድርገህ ብታስብም፣ እግዚአብሔር ግን በእናንተ ውስጥ ውበትን ይመለከታል። እናት ከእርሷ አብራክ የተገኙትን ልጆቿን እንደ ማትረሳ ሁሉ እግዚኣብሔርም እኛን ከቶ አይረሳንም። በሌላ በኩል ደግሞ ከዘጠኝ ወር “እርግዝና” በላይ የሆነና ለዘላለም የሚዘልቅ ዘላለማዊ የሆነ ፍቅር አለ።
ለአንድ ክርስቲያን መጸለይ ማለት በቀላሉ "አባት" ብሎ መናገር ማለት ነው።
እኛም ልክ ጠፍቶ እንደ ተገኘው ልጅ ከእግዚኣብሔር ርቀን የተጓዝን መስሎን ሊሰማን ይችል ይሆናል፣ ወይም ደግሞ በዓለም ውስጥ ተረስቶ እንደተተወ ሰው ሆነን እንዲሰማን የሚያደርገን ብቸኝነት መቋቋም አቆቶን ሊሆን ይችላል፣ እንደገና ስህተትን በመሥራት እና በጥፋተኝነት ስሜት ውስጥ ገብተን ሽባ ሆነን ሊሆን ይችላል። በእነዚያ ዓይነት አስቸጋሪ ጊዜዎች እና ሁኔታዎች ውስጥ በምንገባበት ወቅት ሁል "አባ" ከሚለው ቃል ጀምረን ለመጸለይ የሚያስችል ጥንካሬ አሁንም ማግኘት እንችላለን። ፊቱን ከእኛ አያርቅም፣ በዝምታ ሆኖ አይመለከተንም፣ እርሱ እያየን እንዳላየን ፈጽሞ አይሆንም፣ ሁልጊዜም እዚያው ይገኛል ለእኛ ያለው ፍቅር ታማኝ እንደሆነ ይነግረናል።


 

16 January 2019, 14:29