ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በቫቲካን የቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በቫቲካን የቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ 

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በታኅሳስ 14/2011 ዓ.ም ያስተላለፉት መልእክት

ከመልኣከ እግዚኣብሔር ጸሎት በኋላ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በትላንትናው እለት ማለትም በታኅሳስ 14/2011 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን በእለቱ በተነበበው ቅዱስ ወንጌል ላይ ተመርኩዘው አስተንትኖ ካደርጉ በኋላ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም ክብር በመስጠት ከሚደገሙ ጸሎቶች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀሰውን “የእግዚኣብሔር መልኣክ ማርያምን አበሰራት” የሚለውን የብስራተ ገብሬል ጸሎት ከምዕመናን ጋር በመቀባበል ከደገሙ በኋላ እንደ ተለመደው ለዓለም ባስተላለፉት ሳምንታዊ መልእክት እንደ ገለጹት በቅርቡ በእንዶኔዢያ የተከሰተው ሱናሚ ባስነሳው የባሕር ላይ አውሎ ንፋስ በተጎዱ ሰዎች ማዘናቸውን ቅዱስነታቸው ገልጸዋል።
በዚህ የተፈጥሮ አደጋ ነፍሳቸውን ላጡ ሰዎች እና ዘመድ አዝማዶቻቸውን በጸሎት እንደ ሚያስቡ የገለጹት ቅዱስነታቸው በዚህ የተፈጥሮ አደጋ ምክንያት ጉዳት የደረሰባቸውን እና በስቃይ ውስጥ ያሉትን ሰዎች ሁሉ ቅዱስነታቸው በጸሎት እንደ ምያስቡዋቸው ጨምረው ገልጸዋል። በዚህ የተፈጥሮ አደጋ ምክንያት በንብረትም ላይ ከፍተኛ የሆነ ጉዳት በመድረሱ የተነሳ ሁላችንም የተቻለንን ቁሳዊ ድጋፍ እንድናደርግ ጥሪ አቀርባለው ማለታቸውም ተገልጽዋል።
የገናን በዓለ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ለማክበር በማሰብ በአሁኑ ወቅት ከተለያዩ አከባቢዎች የመጡ ሰዎች በአንድነት በመሰባሰብ ላይ መሆናቸውን የገለጹት ቅዱስነታቸው ይህም በቤተሰብ ውስጥ ያለውን አንድነት ተጠብቆ እንዲሄድ የሚያደርግ ተግባር በመሆኑ የተነሳ ይህ መልካም ባሕል ተጠብቆ ይሄድ ዘንድ መንፈሳዊ በሆነ መልኩ የገናን በዓል ማክበር ያስፈልጋል ብለዋል።
ቅዱስነታቸው በመልእክታቸው ማብቂያ ላይ እንደ ገለጹት ይህንን የገናን በዓል በምናከብርበት ወቅት ይህንን በዓል በሚገባ ለማክበር ያልቻሉ ወገኖቻችንን በማሰብ የተቻለንን በጎ ተግባር በመፈጸም፣ እጆቻችንን በመዘርጋት ልናከብር እንደ ሚገባው የገለጹት ቅዱስነታቸው በወቅቱ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን፣ መንፈሳዊ ነጋዲያን እና እንዲሁም ለመላው ክርስቲያኖች መልካም የገና በዓል ይሆን ዘንድ ተመኝተውና እንደ ተለመደው “እባካችሁን ለእኔ መጸለይ በፍጹም እንዳትዘነጉ” በማለት ከተማጸኑ በኋላ ሐዋርያዊ ቡራኬያችውን ሰጥተው መሰናበታቸውን ለመረዳት ተችሉዋል።
 

24 December 2018, 16:26