2018.11.21  GMG PANAMA - Conferenza Episcopale Panama 2018.11.21 GMG PANAMA - Conferenza Episcopale Panama 

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በፓናማ በሚካሄደው 34ኛው ዓለማቀፍ የወጣቶች ቀን ላይ እንደ ሚሳተፉ ተገለጸ።

“እነሆኝ የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ ” (ሉቃ 1፡38)

ከጥር 15-19/2011 ዓ.ም “እነሆኝ  የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ ” (ሉቃ 1፡38) በሚል መሪ ቃል 34ኛው ዓለማቀፍ የወጣቶች ቀን በፓናማ እንደ ሚከበር ይታወቃል። በዚህ በፓናማ በሚካሄደው 34ኛው ዓለማቀፍ የወጣቶች ቀን ላይ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እንደ ሚገኙ ለመረዳት ተችሉዋል። በዚህ መሰረት ለቅዱስነታቸው ከወጣው የጉዞ መረሃ ግብር ለመረዳት እንደ ተቻለው ቅዱስነታቸው ረቡዕ ጥር 15/2011 ዓ.ም በሮም ከተማ ከሚገኘው እና በሊዮናርዶ ዳቪንቺ ስም ከተሰየመው ዓለማቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ተነስተው በፓናማ በሚገኘው ቶኩሜን ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንደ ሚደርሱ ከቅድስት መንበር የህትመት እና የዜና ክፍል ካወጣው መረጃ ለመረዳት ተችሉዋል።

የዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ሐሙስ ጥር 16/2011 ዓ.ም

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በፓናማ ብሔራዊ ቤተ መንግሥት በመገኘት ከሀገሪቷ ርዕሰ ብሔር እና ከምንግሥት ባለስልጣናት ጋር ይገናኛሉ። ከዚያ በመቀጠል ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ከተለያዩ ከመካከለኛው አሜሪካ ከተውጣጡ ብጹዕን ጳጳሳት ጋር ይገናኛሉ።

ዐርብ ጥር 17/2011 ዓ.ም

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በፓናማ የሚገኘውን የወጣቶች መዓከል ይጎበኛሉ፣ በዚያ የሚካሄደው የምስጢረ ንስሐ ስነ-ስረዓት ላይ ይሳተፋሉ። በተመሳሳይ ቀን ከሰዓት በኋላ ላይ ወጣቶች በፓናማ ከተማ በሚያደርጉት የወጣቶች የመስቀል መንገድ ጸሎት ላይ ቅዱስነታቸው እንደ ሚሳተፉ ከወጣው የጉዞ መረሃ ግብር ለመረዳት ተችሉዋል።

ቅዳሜ ጥር 18/2011 ዓ.ም

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በፕናማ ከተማ በሚገኘው የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ባዚሊካ ውስጥ መስዋዕተ ቅዳሴ ያሳርጋሉ። ከመስዋዕተ ቅዳሴ ስነ-ስረዓት በመቀጠል ቅዱስነታቸው ከወጣቶች ጋር የምሳ ግብዣ ይቋደሳሉ። አመሻሹ ላይ ቅዱስነታቸው ወጣቶች ባዘጋጁት የዋዜማ የጸሎት ፕሮግራም ላይ ይገኛሉ፣ ከወጣቶች ጋር በጋራ ጸሎት ያደርሳሉ።

እሁድ ጥር 19/2011 ዓ.ም

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በፓናማ ከተማ በርካታ ወጣቶች በተገኙበት መስዋዕተ ቅዳሴን ያሳርጋሉ። በመቀጠል ደጉ ሳምራዊ በመባል የሚታወቀውን ተቋም ከወጣቶች ጋር በመሆን ይጎበኛሉ። ከዚያም አመሻሹ ላይ ቅዱስነታቸው ወደ ሮም እንደ ሚመለሱ ለዚህ ለ34ኛው ዓለማቀፍ የወጣቶች ቀን ከወጣው የጉዞ መረሃ ግብር ለመረዳት ተችሉዋል።

22 November 2018, 14:15