2018.08.01 Udeinza Generale 2018.08.01 Udeinza Generale 

የመጀመሪያ ትዕዛዝ ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ አታምልክ የሚል ነው

እኛ ክርስቲያኖች፣ በእውነት የምናመልከው ኣምላክ የቱ ነው ብለን ልንጠይቅ ያስፈልጋል። ጣኦቶች ሕይወትን ይወስዱብናል እንጂ ሕይወትን አይሰጡም። እውነተኛው አምላክ ሕይወትን ይሰጣል እንጂ ሕይወትን አይወስድም። እግዚአብሔር የማይሆን እድል እንደሚገጥመን ከመንገር ይልቅ በእጃችን የያዝነውን መልካም እድል እንድንወድ ያስተምረናል። እግዚአብሔር የሚወደውን ልጁን ለእኛ ሲል አሳልፎ ሰጠ እንጂ ልጅ ከቤተሰብ ነጥሎ አይወስድም።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኮንን - ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ ዘወትር ረዕቡ እለት በቫቲካን በሚገኘው የጳውሎስ 6ኛ የስብሰባ አዳራሽ ወይም ደግሞ እዳስፈላጊነቱ እና እንደ አየሩ ሁኔታ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለሚሰበሰቡ ምዕመናን እና የሀገር ጎብኝዎች በተለያዩ አርእስቶች ላይ ተመርኩዘው የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ ይታወቃል።በእዚህ መሰረት በሐምሌ 25/2010 ዓ.ም ያደርጉት የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ በጣኦት አምልኮ ዙሪያ ላይ ትኩረቱን ያደርገ ሲሆን በዚህ አስተምህሮ የሰው ልጅ ያለ አንድ መሠተዊ ነገር መኖር አይችልም። ይህ ዓለም፣ በጣኦት ደረጃ የሚታዩትን በርካታ ቁሳ ቁሶችን፣ ምስሎችን፣ ሃሳቦችንና ሃላፊነቶችንና ጸሎቶችን የሚያቀርብልን ለዚህ ነው። እኛ ጸሎታችንን ማቅረብ ያለብን ወደ አባታችን ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ነው ማለታቸውን ለመረዳት ተችሉዋል። ከዚህ ቀጥሎ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮ በጣኦት አምልኮ ዙሪያ ያቀረቡትን አስተምህሮ ትርጉም ሙሉ ይዘት እንደሚከተለው አቅርበነዋል። 

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንዴት አረፈዳችሁ፣

"የመጀመሪያ ትዕዛዝ የሆነውን እና ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ" (ከኦ.ዘ. 20:3) አታምልክ የሚለውን ሲነበብ ሰምተናል። ከጣዖት አምልኮ አኳያ ወቅታዊነት ስላለው በዚህ ላይ ማተኮር መልካም እና ጠቃሚ ይሆናል።

ይህ ትዕዛዝ ጣኦትን እንዳናመልክ፣ እንደ ጣኦትም ሊመለኩ በሚችሉ በማንኛውም ምስል እና የጊዜው እውኔታ ላይ እንዳንመካ ያስጠነቅቀናል። የሚያምኑትን ሆነ የማያምኑትን የማይጠቅም የሰው ልጅ ዝንባሌንም ያካትታል። ለምሳሌ እኛ ክርስቲያኖች፣ በእውነቱ እኛ የምናመልከው እግዚአብሔር የቱ ነው ብለን ልንጠይቅ እንችላለን። "አምልኮተ ጣኦት የተሳሳተ አረማዊ አምልኮን የሚመለከት ብቻ አይደለም። አምልኮተ ጣኦት የአምላክን ልዩ ጌትነት ስለማይቀበል ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖረንን ሕብረት የሚቃረን ነው" (የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ትምሕርተ ክርስቶስ ቁ. 2113 ላይ እንደተገለጸው).

በነባራዊ እቅድ ውስጥ እግዚአብሔር ምንድን ነው? እግዚአብሔር የግል ሕይወታችን መሠረት በመሆኑ የምናስባቸው እና የምናደርጋቸው በሙሉ መነሻቸው እርሱ ነው። ወንጌልን መሠረቱ ባላደረገና በስም ብቻ ክርስቲያን በሚባል ቤተ ሰብ ውስጥ ማደግ ይቻላል። የሰው ልጅ ያለ አንድ መሠተዊ ነገር መኖር አይችልም። ይህ ዓለም፣ በጣኦት ደረጃ የሚታዩትን በርካታ ቁሳ ቁሶችን፣ ምስሎችን፣ ሃሳቦችንና ሃላፊነቶችንና ጸሎቶችን የሚያቀርብልን ለዚህ ነው። እኛ ጸሎታችንን ማቅረብ ያለብን ወደ አባታችን ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ነው። በአርጀንቲን እያለሁ ወደ አንድ ቁምስና መሄዴን አስታውሳለሁ። የሄድኩትም ለዚህ ቁምስና ምዕመናን ምስጢረ ሜሮን ለማደል ነበር። ወደዚህ ቁምስና ስጓዝ አንድ ጫካ ማቋረጥ ነበረብኝ። በዚህ ጫካ ውስጥ የተመለከትኩት ነገር ቢኖር ከሃምሳ የሚበልጡ ሰዎች በየወንበሮቻቸው ፊት ለፊት ተቀምጠው የመጫወቻ ካርታ ሲያገለባበጥ ተመለከትኳቸው። በቦታው የተሰባሰቡበት ምክንያት የጣኦት አምልኮን ለማድረግ ነበር። የወደ ፊት ሕይወታቸው መሪ የሆነውን እግዚአብሔር ከማምለክ፣ ወደ እርሱ ጸሎታቸውን ከማቅረብ ይልቅ፣ የወደ ፊት ሕይወታቸውን እጣ ፈንታ ከመጫወቻ ካርታ ይረዱ ነበር። እንግዲህ ይህ ዛሬ ዓለማችን የሚያቀርብልን የጣኦት አምልኮ ነው። እስቲ አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ። ስንቶቻችሁ ናችሁ የወደ ፊት ሕይወታችሁ ምን ይመስል እንደሆነ ለማወቅ ብላችሁ ወደ ሞራ ገላጭ ዘንድ ሄዳችኋል። ስንቶቻችሁ ናችሁ የወደ ፊት ሕይወታችሁ ምን ይመስል እንደሆነ ለማወቅ ብላችሁ፣ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ከመጸለይ  ይልቅ የእጅ አሻራዎቻችሁን አስነብባችኋል። በእነዚህ ሁለቱ አምልኮዎች መካከል ያለው ልዩነት ይህ ነው። እኛ ክርስቲያኖች ሕያው እና ጊዜ የማይሽረው አምልክ አለን። የተቀረው በሙሉ የማጠቅም ጣኦት ነው።

የጣኦት አምልኮ የሚያድገው እንዴት ነው ቢባል፥ በኦሪት ዘ ጸዓት በምዕ. 20፤4 ላይ እንደተጻፈው በማንበብ መልስ ማግኘት እንችላለን። እንዲህ ተጽፎ እናገኘዋለን፦ በላይ በሰማይ ካለው፥ በታችም በምድር ካለው፥ ከምድርም በታች በውኃ ካለው ነገር የማናቸውንም ምሳሌ፥ የተቀረጸውንም ምስል ለአንተ አታድርግ ይላል።

ጣኦት የሚለው ቃል መሠረቱ ከግሪክ ቃል በመሆኑ እና እንደ ግሪኮች አገላለጽም ማየት የሚለውን ግስ ይወክላል። ጣኦትም በተቀረጹት ምስሎች የተመሠረተ በመሆኑ የሰውን እይታ ከሚያዙ እና ከሚጨበጥ ግዙፍ አካላት ጋር ያዛምዳል። ይህን መንገድ ከሚከተሉት የዘመናችንን የማስታወቂያ ሥራዎችን ያየን እንደሆነ፣ በማስታወቂያው በኩል በገበያ ላይ የዋሉትን ሸቀጣ ሸቀጦች፣ መኪኖችን ወይም ተንቀሳቃሽ ስልኮችን በአካል ባንመለከታቸውም ፍላጎቶቻችንን እንደሚያሟሉልን በዓይነ ሕሊና ብቻ በመቀበል እንመኛቸዋለን፣ እናወራቸዋለን ከዚያም አልፎ ተርፎ ፍላጎታችንን እንደሚያረኩን፣ ደስታን እንድሚሰጡን በማመን የግል ንብረት ለማድረግ እንጥራለን።

በኦሪት ዘጸዓት ምዕ። 20:4 ላይ የተጠቀሰውን ሁለተኛውን ክፍል ስንመለከት የማናቸውንም ምሳሌ፥ የተቀረጸውንም ምስል ለአንተ አታድርግ የሚለውን እናገኛለን። ጣዖቶች በሙሉ የአምልኮ ሥርዓቶችን አዘጋጅተው እንዲመለክላቸው እና እንዲሰገድላቸው ይፈልጋሉ። ጣኦቶች በድሮ ዘመን፣ አሁንም ቢሆን ሰው በመስዋዕትነት ይቀርብላቸዋል። ስንት ሰዎች ቁንጅናቸውን ለማሻሻል ብለው ሲኳኳሉ ይውላሉ። መኳኳል ስህተት አይደለም ነገር ግን በአግባቡ ሲሁን ያምራል። ነገር ግን ከሰው አፈጣጠር በልጦ እና ሌላ ምስሎ መቅረብ ራስን ወደ ጣኦትነት ሊመራ ይችላል። አያችሁ እንግዲህ፣ ጣኦት ሰዎች ራሳቸውን እንደ ጣኦት እንዲያቀርቡ፣ ገንዘባቸውንና ሕይወታቸውን በመስረቅ፣ ለጊዜያዊ ደስታ ራሳቸውን አስልፈው እንዲሰጡ ያደርጋል። አንዳንድ የምርት ማምረቻዎች ተቋማት ወይም ፋብሪካዎች በርካታ ሰዎችን ከሥራ ሲያሰናብቱ እናያለን። በዚህም የተነሳ ብዙ ሰዎች ሥራ ፈት ይሆናሉ። ይህን የሚያደርጉበት ዋናው ምክንያት የበለጠ የገንዘብ ትርፍ ለመሰብሰብ ነው። ይህ ደግሞ ገንዘብን እንደ ጣኦት እንዲያመልኩ ያደርጋቸዋል። የዚህ ትርፉ የበርካታ ቤት ሰብ ሕይወት እንዲበላሽ፣ ሥራ የፈቱ በርካታ ወጣቶች አደንዛዥ ዕጾችን በመውሰድ ለጉዳት ይዳረጋሉ። አደንዛዥ ዕጽ በራሱ አንድ ጦት ነው።

በሦስተኛ ደረጃ፣ አንተም እነዚህን ጣኦቶች አታገለግላቸው ወይም ባሪያ አትሁናቸው የሚለው ነው። በእርግጥ ጣኦቶች ባሪያ ያደርጋሉ። ደስታን ለመስጠት ቃል ይገባሉ ነገር ግን ቃላቸውን ተግባራዊ አያደርጉም። ፈጽሞ በማናገኛቸው ነገሮች ላይ ተስፋን በማድረግ ሕይወታችንን በሙሉ እናባክናለን።

ወድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ ጣኦቶች ሕይወትን ይወስዳሉ እንጂ ሕይወትን አይሰጡም። እውነተኛው አምላክ ሕይወትን ይሰጣል እንጂ ሕይወትን አይወስድም። እግዚአብሔር የማይሆን እድል እንደሚገጥመን ከመንገር ይልቅ በእጃችን የያዝነውን መልካም እድል እንድንወድ ያስተምረናል። እግዚአብሔር የሚወደውን ልጁን ለእኛ ሲል አሳልፎ ሰጠ እንጂ ልጅ ከቤተሰብ ነጥሎ አይውወስድም። ስለዚህ ዛሬ የምጋብዛችሁ ስንት ጣኦቶች አሉኝ ወይም ለእኔ የተመረጠ ጣኦት የትኛው ነው ብላችሁ ራሳችሁን እንድትጠይቁ ነው። ይህን ለይቶ ማወቅ ወደ ፍቅር ጎዳና የሚመራ ጸጋ ነውና። እውነተኛ ፍቅር ከጣኦት ጋር ግንኙነት የለውም። አንድ ነገር የማይዳሰስ እና የማይጨበጥ ከሆነ ከልጅ፣ ከጓደኝነትም በላይ ይሆናል። ስለዚህ ፍቅርን አጥብቀን እንያዝ። ወደ ጣዖቶች ለመመለስ ብለን በጣም ውድ የሆኑትን አባትን፣ እናትን፣ ልጆችን፣ ሚስትን፣ ባልን፣ ቤተሰብ መተው አያስፈልግም። ስለዚህ ጣኦቶችን በሙሉ አውልቀን በመጣል ነጻ መሆን ያስፈልጋል።" 

        

01 August 2018, 16:04