“ቤተሰብ ዛሬም ለዓለም መልካም ዜና መሆኑን ቀጥሉዋል ወይ “ቤተሰብ ዛሬም ለዓለም መልካም ዜና መሆኑን ቀጥሉዋል ወይ 

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ቤተሰብ ለዓለም ምልካም ዜና መሆኑን ቀጥሉዋል።

በየደረጃው ለሕይወት ራሱን ክፍት ያደረገ፣ በአንድ ወንድ እና በአንድ ሴት ኅብረት ላይ የተመሰረተ ቤተሰብ፣ በዓለም ውስጥ መልካም ዜና ሆኖ መኖሩን ቀጥሉዋል

“በየደረጃው ለሕይወት ራሱን ክፍት ያደረገ፣ በአንድ ወንድ እና በአንድ ሴት ኅብረት ላይ የተመሰረተ ቤተሰብ፣ በዓለም ውስጥ መልካም ዜና ሆኖ መኖሩን ቀጥሉዋል” ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ ከነሐሴ 15-20/2010 ዓ.ም በደብሊን ከተማ ለሚካሄደው ዓለማቀፍ የቤተሰብ ጉባሄ ዝግጅት ይሆን ዘንድ በመጋቢት 21/2009 ዓ.ም. ከአስተላለፉት መልእክት የተወሰደ ነው።

የዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃይሌጊዮርጊስ-ቫቲካን

አንደ አውሮፓዊያኑ የቀን አቆጣጠር ከነሐሴ 15-20/2010 ዓ.ም በደብሊን ከተማ የሚካሄደው ዓለማቀፍ የቤተሰብ ጉባሄ “የቤተሰብ መልካም ዜና ለዓለም ደስታ” በሚል መሪ ቃል እንደ ሚካሄድ ከወዲሁ የተገለጸ ሲሆን በመጋቢት 20/2009 ዓ.ም. በቅድስት መንበር የሕትመት ቢሮ ከተሰጠው መግለጫ ለመረዳት እንደቻልነው የቤተሰብ ሕይወት ይበልጡኑ ይጠናከር ዘንድ ቅዱስነታቸው እ.አ.አ በመጋቢት 19/2016 ዓ.ም. ለንባብ ያበቁት በላቲን ቋንቋ “አሞሪስ ላይቲሲያ” በአማሪኛው በግርድፉ ሲተረጎም “የፍቅር ሐሴት” በሚል አርእስት ይፋ ያደርጉት ሐዋሪያዊ ቃለ ምዕዳን በቤተሰብ ውስጥ ሊኖር ስለሚገባው ፍቅር የሚተነትን ቃለ ምዕዳን በመሆኑ የቤተሰብ አባላት በዚህ ቃል ምዕዳን ውስጥ የተጠቀሱትን ቁምነገሮች በመጠቀም ሕይወታቸውን ማጠናከር እንደ ሚገባቸውም ተጠቅሱዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ ከነሐሴ 15-20/2010 ዓ.ም በደብሊን ከተማ ለሚካሄደው ዓለማቀፍ የቤተሰብ ጉባሄ ያስተላለፉት መልእክት በሁለት ጥያቄዎች ላይ መሰረቱን ያደረገ ነበር። በቀዳሚነት የተቀመጠው “ቅዱስ ወንጌል ለዓለም የደስታ ምንጭ ሆኖ እየቀጠለ ነው ወይ?” የሚለው ጣይቄ እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ቅዱስነታቸው ያቀረቡት ጥያቄ  “ቤተሰብ ዛሬም ለዓለም መልካም ዜና መሆኑን ቀጥሉዋል ወይ”? የሚለውን ጥያቄ ደግሞ ቅዱስነታቸው ያነሱት ጥያቄ ነው።

ቤተሰብ ለዓለም መልካም ዜና ነው!

“እኔ እንደማስበው ቤተሰብ ዛሬም ቢሆን ለዓለም መልካም ዜና መሆኑ እየቀጠለ ያለ ይመስለኛል” ያሉት ቅዱስነታቸው ይህም አዎንታዊ አስተሳሰብ የመነጨው ቤተሰብ መሰረቱን በእግዚኣብሔር ላይ ያደርገ በመሆኑ የተነሳ ነው ብለዋል።

የእግዚኣብሔር ፍቅርና የእርሱ “አዎንታ” የፍጥረታት ሁሉ ልብ ውስጥ ይገኛል ያሉት ቅዱስነታቸው ይህም “አዎንታ” ራሳቸውን በየደረጃው በሕያወት ውስጥ ለሚያጋጥማቸው መንፈሳዊ አገልግሎቶች ክፍት ባደረጉ ወንድ እና ሴት ኅብረት ውስጥም ይነጸባረቃል ብለዋል።

የእግዚኣብሔር “አዎንታዊ” ምላሽ በተለይም ደግሞ በተለያዩ ነገሮች ልባቸው ለቆሰለ፣ ለተበደሉ፣ ፍቅርን ያላጣጣሙ ሰዎችን ሁሉ ለመርዳት እና ለመደገፍ ዝግጁ ነው ያሉት ቅዱስነታቸው ቤተሰብ “አዎንታዊ የእግዚኣብሔር ፍቅር” የሚገለጥበት ስፍራ ነው ብለዋል።

ቤተሰብ በእግዚኣብሔር ላይ መሰረቱን ሊያደርግ ይገባዋል!

“ቤተሰብ በዚህ የእግዚኣብሔር ፍቅር ላይ መሰረቱን ሲያደርግ ብቻ ነው በዓለም ውስጥ የእግዚኣብሔ ፍቅር ዳግም እንዲፈጠር ማድረግ እና የእግዚኣብሔርን ፍቅር መግለጽ የሚችለው በዚሁ መንገድ ብቻ ነው፡ ያለ እግዚኣብሔር ፍቅር እንደ እግዚኣብሔር ልጅ፣ እንደ ቤተሰብ እና እንደ እህት ወንድም ሆኑ መኖር በፍጹም አይቻልም”።

ቅዱስነታቸው ይህንን አጋጣሚ ተጠቅመው በዓለም ዙሪያ ለሚገኙ የቤተሰብ አባላት ራሳቸውንና ሕይወታቸውን እንዲፈትሹ በማሰብ የምትኖሩት ሕይወት “በእግዚኣብሔር ፍቅር ላይ መሰረቱን ያደረገ ነው ወይ? በፍቅር እና ለፍቅር ብቻ ነው የምትኖሩት? የሚለውን ጥያቄ በመጠየቅ የቤተሰብ አባላት ራሳቸውን ሊመረምሩ ይገባል ብለዋል።

የቤተሰብ ሕይወት እንዲጠነክር መትጋት ያስፈልጋል!

“የፍቅር መገለጫ የሆኑ ተግባራትን በምናከናውናቸው እለታዊና ቀላል በሆኑ ተግባራት መግለጽ እንችላለን” ያሉት ቅዱስነታቸው ይህም በቀላሉ “እባክህን፣ አመሰግናለሁ እና ይቅርታ” የሚሉትን ቀለል ያሉ ቃላትን በመጠቀም መግለጽ እንደ ሚቻልም ቅዱስነታቸው በመልእክታቸው ገልጸዋል።

“በእየለቱ በቤተሰብ ውስጥ የሚያጋጥሙትን ተግዳሮቶች፣ ድክመቶችና መታከቶችን ሁሉ ከግምት በማስገባት  የቤተሰብ አባላት እና እኛ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች የሆንን ሁላችን የቤተሰብ ሕይወት ይጠናከር ዘንድ ማስተማር እና መደገፍ ይጠበቅብናል፣ ራሳቸውን መርዳት የማይችሉትን መርዳት፣ በሕይወት ጉዞዋቸው ከእነርሱ ጋር አብሮ መጓዝ፣ በጎ ፈቃድ ያላቸውን ሰዎች ሁሉ በዚህ ተግባር በማሳተፍ የቤተሰብ ሕይወት እንዲጸና እና ሰላማዊ ይሆን ዘንድ መትጋት ያስፈልጋል” ካሉ ቡኃላ መልእክታቸውን አጠናቀዋል።[ Audio Embed በድምጽ የቀረበ ዘገባ ለማዳመጥ ከዚህ በታች ያለውን ተጫወት የሚለውን ምልክት ይጫኑ]

 

17 August 2018, 14:44