ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ዓ.ም በቅድስት ማርታ የጸሎት ቤት መስዋዕተ ቅዳሴ ሲያሳርጉ ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ ዓ.ም በቅድስት ማርታ የጸሎት ቤት መስዋዕተ ቅዳሴ ሲያሳርጉ 

ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በእዚህ ወረርሽኝ ወቅት ለመምህራን እና ተማሪዎች መጸለያቸው ተገለጸ።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በሚያዝያ 16/2012 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው የቅድስት ማርታ የጸሎት ቤት ውስጥ ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ትኩረት ሰጥተው የጸለዩት በአሁኑ ወቅት በመላው ዓለም እየተከሰተ በሚገኘው የኮሮና ቫይረስ ምክንያት በየቤታቸው ውስጥ ተቀምጠው ትምህርታቸውን በመገናኛ ብዙሃን አውታሮች ለመከታተል ለተገደዱትን ተማሪዎች እና መምህራን ጸሎት ያደረጉ ሲሆን “በኢንተርኔት እና በሌሎች ዲጂታል በሆኑ መንገዶች ትምህርት ለመስጠት በጣም ጠንክረው ለሚሰሩ አስተማሪዎች ዛሬ እንጸልያለን፣ እንዲሁም ባለመዱት መንገድ አመታዊ ፈተናዎችን መውሰድ ለተገደዱ ተማሪዎች እንጸልያለን፣ በጸሎት ከእነርሱ ጋር አብረን እንሁን” ብለዋል።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ በተደረገው መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ያደረጉት ስብከት በዕለቱ ከዮሐንስ ወንጌል (6፡1-15) ላይ ተወስዶ በተነበበውና “ኢየሱስም ቀና ብሎ ሲመለከት ብዙ ሕዝብ ወደ እርሱ ሲመጣ አየ፤ ፊልጶስንም፣ “እነዚህ ሰዎች እንዲበሉ እንጀራ ከየት እንግዛ?” አለው። ይህን የጠየቀው ሊፈትነው እንጂ ራሱ ሊያደርግ ያሰበውን ያውቅ ነበር።ፊልጶስም፣ “እያንዳንዱ ሰው ትንሽ ትንሽ እንዲቃመስ ለማድረግ፣ የሁለት መቶ ዲናር እንጀራ እንኳ አይበቃም” ሲል መለሰ። ከደቀ መዛሙርቱ አንዱ፣ የስምዖን ጴጥሮስ ወንድም እንድርያስም፣ እንዲህ አለ፤ “አምስት ትንንሽ የገብስ እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ የያዘ አንድ ልጅ እዚህ አለ፤ ይህ ግን ለዚህ ሁሉ ሕዝብ እንዴት ይዳረሳል?” ኢየሱስም፣ “ሰዎቹ እንዲቀመጡ አድርጉ” አለ። በዚያ ቦታ ብዙ ሣር ነበረ፤ አምስት ሺህ ያህል ወንዶችም ተቀመጡ። ኢየሱስ አምስቱን እንጀራ አንሥቶ አመሰገነ፤ ለተቀመጡትም የሚፈልጉትን ያህል ዐደለ፤ ዓሣውንም እንዲሁ አደረገ” በአምስት ትንንሽ የገብስ እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ” አምስት ሺህ ሰው እንደ መገበ በሚያወሳው የቅዱስ ወንጌል ክፍል ላይ መሰረቱን ያደረገ እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን ኢየሱስ ይህንን ጥያቄ ለፊሊጶስ ያቀረበው ሊፈትነው ፈሎጎ ነው እንጂ እርሱ ራሱ ምን ማድረግ እንዳለበት በትክክል ያውቅ ነበር ብለዋል።

ኢየሱስ በመፈተን አስተምሯል

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ስብከታቸውን ሲቀጥሉ “የዚህ ምንባብ አረፍተ ነገር እንድናስብ ያደርገናል” ያሉ ሲሆን ኢየሱስ ፊሊጶስን ሲጠይቀው በእርሱ በፊሊጶስ አእምሮው ውስጥ “እነዚያ ሰዎች የሚበሉት እንጀራ ከየት መግዛት እንችላለን?” የሚል አሳብ ነበረው ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እንደተናገሩት “ኢየሱስ ሊያከናውን ያሰበውን ያውቃል፣ ፊልጶስን ግን እየፈተነው ነበር፣ በዚህ ትዕይንት ላይ  ኢየሱስ ለሐዋርያቱ የነበረውን ዓይነት አስተሳሰብ ማየት ትችላላችሁ፣ ሊያስተምራቸው ሲፈልግ ሁልጊዜ ይፈትናቸው ነበር፣ እነርሱ ከኢየሱስ የአስተሳሰብ መንገድ ወጣ ሲሉ ወደ ትክክለኛው መስመር እንዲመለሱ እርሱ ያስተምራቸው ነበር” ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ እንደገለጹት ቅዱስ ወንጌል እነዚህን በመሳሰሉ “ደቀ መዛሙርቱ የእግዚአብሔር ህዝብ ጠባቂ ሁነው እንዲያድጉ ለማድረግ እነዚህን በመሳሰሉ ኢየሱስ ከሐዋርያቱ ጋር የነበረው ዓይንት ግንኙነቶች እና ምልክቶች የተሞላ ነው” ብለዋል።

ኢየሱስ በጣም ከሚወዳቸው ነገሮች አንዱ “ከህዝቡ ጋር መሆን ነበር፣ ምክንያቱም ይህ ደግሞ ዓለም አቀፋዊ የሆነ የመዋጀት ምልክት ነው። በወቅቱ ሐዋርያት ከማይወዱት ነገሮች መካከል አንዱ የተሰበሰበ ሕዝብ ማየት ነው፣ ምክንያቱም እነርሱ ብቻ ለጌታ ቅርብ ለመሆን እና እርሱ የሚለውን ነገር ሁሉ ለማዳመጥ እጅግ ይፈልጉ ስለነበር ነው” በማለት በአጽኖት ገልጸዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ስብከታቸውን ሲቀጥሉ ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን ያዳምጡና እርስ በእርሳቸው ይነጋገሩ እንደ ነበረ ያወሱ ሲሆን “ጌታ ከሕዝቡ ጋር የቀረበ ግንኙነት ያለው በመሆኑ የተነሳ የቤተክርስትያን አገልጋዮች የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለማገልገል ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር የቀረበ ግንኙነት መፍጠር ይኖርባቸዋል” ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ኢየሱስ ከህፃናት ጋር የነበረበትን ወቅት በዋቢነት በማንሳት እዚያም ቢሆን ኢየሱስ ሕጻናት የማይረብሹት መሆኑን ደቀ መዛሙርቱ እንዲገነዘቡ ይፈልግ ነበር በእዚህም የተነሳ ሕፃናቱ ወደ እርሱ እንዲመጡ ይፈልግ እንደ ነበር ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ተናግረዋል ፡፡

“ወደ እግዚአብሔር ሕዝብ የሚያቀርበውን ይህንን ሐዋርያዊ የሆነ ባህሪ ለሐዋሪያት አስተምሯቸዋል” ያሉት ቅዱስነታቸው የእግዚአብሔር ሕዝብ አንድን ሰው እንዲደክም ሊያደርጉት ይችላል “ምክንያቱም ሁልጊዜ ተጨባጭ ነገሮችን ስለሚጠይቁ…” ነው፣ እናም የቤተክርስትያን አገልጋዮች እነዚህን ነገሮች ለመማር ሁል ጊዜ ዝግጁ መሆን ይኖርባቸዋል ብለዋል።

ኢየሱስ አምስት ትንንሽ የገብስ እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ በመጠቀም አምስት ሺህ ሰው የመገበበት ሁኔታ በሌላ አቅጣጫ ስንመለከት ቀኑ እየመሸ መምጣቱን የተመለከቱ ሐዋርያት ሕዝቡን ወደ እየመጣበት ለመሸኘት ፈልገው እንደ ነበረ እንደ ሚያሳይ የገለጹት ቅዱስነታቸው ኢየሱስ ግን “የሚበሉትን ነገር ስጧቸው” በማለት ደቀ መዛሙርቱን እንደ ፈተናቸው ገልጸዏል። “ኢየሱስ ዛሬ ለቤተክርስትያን አገልጋዮች ሁሉ እንዲህ ይላል- “የሚበሉትን ስጧቸው፣ አጽኗኗቸው፣ የጠፉ ሰዎች ካሉ መውጫ መንገዱን አሳዩዋቸው” በማለት እንደ ሚናገር ገልጸዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ስብከታቸውን ሲደመደሙ “የቤተክርስትያን አገልጋዮች ስልጣን የተሰጠው ለአገልግሎት ነው ፡፡ ከእዚህ የተለየ ስልጣን የላቸውም። ስልጣናችሁን ለሌላ አግልግሎት መጠቀም ስትጀምሩ ስሕተት መሥራት ትጀምራላችሁ፣ በእዚህም መልኩ ጥሪያችሁን ታበላሻላችሁ” ብለው ከሁሉም በላይ የእግዚአብሔርን ሕዝብ መፍራት ሳይሆን ወደ እነሱ ቅርብ መሆን ይችሉ ዘንድ ለቤተክርስትያን አገልጋዮች ጸሎት ካደረጉ በኋላ ቅዱስነታቸው የእለቱን ስብከት አጠናቀዋል።

24 April 2020, 12:05
ሁሉንም ያንብቡ >