ፈልግ

2023.05.01 Re Davide, il peccatore

ኃጢአት ምንድር ነው?

ኃጢአት የሚለው ቃል አመጣጡ ከግእዝ ነው፡፡ መሠረታዊ ቃሉ «ኃጢእ» ይባላል፡፡ ትርጉሙም ያጣ፣ የተገፈፈ፣ የተነጠቀ ማለት ነው፡፡ ይህም ከእግዚአብሔር በጥምቀት አማካይነት የተሰጠውን የልጅነት ጸጋ ያጣ፣ የተገፈፈ፣ የተነጠቀ ማለት ነው፡፡

ኃጢአት የእግዚአብሔር ቅዱስ ሕግ አውቆ፣ ፈቅዶ በቀጥታ መቃወም ወይም ማፍረስ ማለት ነው፡፡ የመጀመሪያው ሰው አዳም የተከለከለውን ፍሬ አውቆ በመብላቱ የእግዚአብሔርን ሥልጣን በቀጥታ ተቃወመ፣ ቸርነቱንም ረሳ፣ ጸጋውን ናቀ፣ ጥበቡን ነቀፈ፣ ጽድቁንም ካደ፣ የትእዛዝ ቃሉንም አቃለለ (ዘፍ.3፡1-6)፡፡ ኃጢአት ማለት በልዑል እግዚአብሔር ላይ ማመጽ፣ በቅዱስ አመራሩ ሥር አለመሆን፣ መሎኮታዊ ጥሪውንም አለማዳመጥ ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የመጀመሪያውን ሰው ሲፈጥር ግብ ነበረው፣ ዓላማም ነበረው፡፡ ሆኖም ያ ዓላማ በኃጢአት ምክንያት ተበላሸ፤ ከዚህም የተነሣ ሰው ወደ አስቸጋሪና አስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ ገባ፡፡ ለክርስቶስ ምስጋና ይግባውና የሰው ልጅ በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ወደ እግዚአብሔር አብ ቀርቦ የኃጢአቱን ይቅርታ እንዲያገኝ ተጋብዞአል፤ «ኃጢአታችንን ለእግዚአብሔር ብንናዘዝ እርሱ ታማኝና ጻድቅ ስለሆነ ኃጢአታችንን ሁሉ ይቅር ይላል» (1ዮሐ.1፡9)፡፡ እንዲሁም «ኃጢአቱን የሚሰውር አይለማም፤ የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምሕረትን ያገኛል» ተብሏል (ምሳሌ.28፡13)፡፡

ንስሐ መግባት ማለት የልብና የአእምሮ መለወጥ፣ አኗኗርንና አካሄድን ከእግዚአብሔር ፈቃድና ከወንጌል እውነቶች ጋር ማስማማት፣ አሮጌ ማንነትን በመቀየር አዲስና የተሻለ ሕይወት ለመጀመር ቁርጥ ፈቃድ ማድረግ ነው፡፡ ያኔ በተጠመቅንበት ጊዜ በእያንዳንዳችን ልብ ወስጥ የተዘራውን መልካም ዘር እንዳያድግ ፍሬ እንዳይሰጥ አንቆ የያዘውን እሾህና አረም ነገሮችን ነቅሎ መጣል ነው፡፡ ንስሐ መግባት ማለት በጌታ ፊት እምነታችንን፣ ደካማነታችንን፣ ተሰባሪዎች መሆኖችንን አምነን ከልዑል እግዚአብሔር ብርቱ እጅ ሥር ራሳችንን ዝቅ ማድረግ፣ ማዋረድና ጸጋንና ኃይልን ወደ ሚያስታጥቀን ቸር አባት ልባችንን ከፍ ማድረግና ምህረቱንም መለመን ነው፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምድራዊ አገልግሎቱን ሲጀምር «መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ» (ማር.1፤15) በማለት የሰበከው የክርስትና ሕይወት ብርሃን በሰው ልጆች ውስጥ የሚጀምረው በንስሐ መሆኑን ለማስተማር ነው፡፡ ንስሐ በመግባት ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት ስለሚቻል ጌታችን ንስሐ ግቡ አለ፡፡ በንስሐ የሕይወት ምርጫችንና ዋስትናችን ወደ ሆነው አምላክ መመለስ ያስፈልገናል፡፡ ከራስ ወዳድነት፣ ከክፉ መሻቶችና በውስጣችን ጠንካራ ሥር ከሰደደው ከኃጢአት ሥራዎች ጋር በርትተን መታገል፣ ጠንካራ ጦርነትን ማካሄድ ይኖርብናል፡፡ ኃጢአትን ብንሸፍንና ብናባብል፤ መልካም እንደሆነ አድርገን ለሕሊናችን ብናቀርብ በእግዚአብሔር ዘንድ የኃጢአትነትን ይዘት በፍጹም አይለቅም፡፡ የሸራሪት ትልቅ ትንሽ የለም ሁሉም ድር መሥራት ይችላል፡፡ እባብም ቢሆን እንደዚው ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል «ኃጢአት አልሠራንም ብንል እግዚአብሔርን ሐሰተኛ እናደርገዋለን፤ ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም» ይላል (1ዮሐ.1፡8-10)፡፡ እንዲሁም «ኃጢአትህን ለመደበቅ ብትሞክር በኑሮህ ሁሉ ነገር አይቃናልህም፤ ኃጢአትህን ተናዝዘህ ዳግመኛ ኃጢአት ከመሥራት ብትቆጠብ ግን የእግዚአብሔር ምህረት ታገኛለህ» ብሏል (ምሳሌ.28፡13)፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም የመጣው ኃጢአትን ይቅር ለማለትና ከኃጢአት የተነሣ በሰዎች መካከል የሚፈጠሩ የሻከሩ ግንኙነቶችን ለመጠገን ነው፡፡ እርሱም ደቀመዛሙርቱን በስሙ ኃጢአትን ይቅር እንዲሉ ባዘዛቸው ጊዜ የማዳንና የማስታረቅ አገልግሎቱን እንድትቀጥል ለቤተክርስቲያኑ ሥልጣን ሰጣት፡፡ «መንፈስ ቅዱስ ተቀበሉ፡፡ ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፣ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል» (ዮሐ›20፡23)፡፡ ዛሬ ምሥጢረ ንስሐን ለመቀበል ከሁሉ የተሻለው ዝግጅት በኢየሱስ ክርስቶስና በቤተክርስቲያን አስተምህሮ አንጻር በጸሎት መንፈስ ህሊናን መመርመር ነው፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ረድኤት እየታገዙ በታማኝነት ህሊናን መመርመር በሕይወታችን ውስጥ የኃጢአታችንን ምክንያት ያደረግነውን ማናቸውንም ጉዳት እንድንክስ ይቀሰቅሰናል፡፡

ቤተክርስቲያናችን እምነት ጉዞ ንስሐ ጥልቅ ታሪክ አለው፡፡ በመጀመሪያዎቹ ምዕተ ዓመታት ምሥጢረ ንስሐ ይሰጥ የነበረው በዕድሜ ውስጥ በጣም ውስን ጊዜ ብቻ ነበር፤ ይኸውም በጣም ከባድ ኃጢአቶች ብቻ ነበር፡፡ ኃጢአተኛውን ከእግዚአብሔርና ከክርስቲያን ወንድሞቹና እህቶቹ የመገለሉ ከባድነት እንዲሰማው ለማድረግ የረዥም ጊዜ ንስሐ መግባትን ያካትት ነበር፡፡ ከጊዜ በኋላ፣ ይህን ምሥጢር የመቀበል ሌላኛ መንገድ ማለትም በካህን ፊት የተደጋገመ፣ ግላዊና ታማኝ ኑዛዜ የማድረግ ሁኔታ ስለታመነበት ተወሰነ፡፡ ይህም የንስሐ ዘዴ ካህኑ ኃጢአተኛውን ሁነኛ የንስሐና የፍቅር ምልክት የሆነውን የንስሐ ቅጣት እንዲመርጥ ይረዳዋል፡፡ ካህኑ እንደ ጌታ ወኪል ሆኖ ያገለግላል፣ በቤተክርስቲያን ስም ቃለ ፊታት ይሰጣል፡፡ ካህኑ እጆቹን በኃጢአተኛው ራስ ላይ አድርጎ «በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም ከኃጢአትዎ እፈታዎታለሁ» የሚሉ ቃላት ሲደግም፣ ሰው እንደመሆናችን ኃጢአታችን እንደቀረልን የምናውቅበትን ምልክት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ይሰጠናል፤ (እምነታችን፤ገጽ.213-215) ራሱም ለደቀ መዛሙርቱ «በእውነት እላችኋለሁ፤ በምድር የምታስሩት በሰማይ የታሰረ ይሆናል፤ በምድር የምትፈቱትም በሰማይ የተፈታ ይሆናል» (ማቴ.18፡18) ብሎ ሥልጣን የሰጠቸው ስለሆነ ዛሬም የእርሱ አገልግሎት ቃል ቤተክርስቲያን ለክርስቶስ አገልግሎት በለየቻቸው ካህናት ዘንድ ይፈጸማል፡፡

ምንጭ፡ አ ባ  ኃ ይ ለ ማ ር ያ ም  ወ ራ ቆ

19 May 2023, 13:19