ፈልግ

ስብከተ ገና ስብከተ ገና  

ስብከተ ገና

የጎርጎርሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል ለማከብር ዝግጅት የሚደረግበት የስብከተ ጋና ወቅት በኅዳር 19/2014 ዓ.ም መጀመሩ ይታወቃል። ስብከተ ገና ኢየሱስ በዓለም ታሪክ ውስጥ በመግባት የዓለምን የቀን አቆጣጠር ወደ ዓመተ ምሕረት እንደቀየረው ሁሉ የእኛንም ሕይወት በምሕረቱ ሊሞላት እንደ ሚመጣ እና በእርሱ በኩል ሁሌም ዝግጁ መሆኑ የሚሰበክበት ወቅትና፣ እኛም ለእዚህ ጌታ ለሚያደርግልን መንፈሳዊ ለውጥ የማምጣት ጥሪ በቃላት እና በትግባር በተደገፈ መልኩ ምላሽ የምንሰጥበት ወቅት ላይ እንገኛለን።

መግቢያ

የገና ምስጢር እና አስደናቂነት እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያሳየው በአክብሮትና በንጽህና የተሞላ ፍቅር ዓመታዊ ማስታወሻዎች ናቸው። የእግዚአብሔርን ልጅ በዚያች የድሆች ከተማ በሆነችው ቤተልሔም ውስጥ መምጣት አስደናቂ እውነታ ለጥቂት ጊዜ ቆም ብለን በአትኩሮት ስናስብ ከራሳችን ማንነትና ዙሪያችንን ከከበቡን ጉዳዮቻችን ሁሉ ለመውጣት እንገደዳለን። ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስና ለእግዚአብሔር አብ አዳኝ ፍቅርና መለኮታዊ ጥበቃ ምስጋና ወደ ማቅረብ አዲስ አድናቆት ወደ መቸር ከፍ ከፍ እንላለን፡፡

የስብከተ ገና ወራት የመታደሻ፣ አዲስ እምነት የመቀበያና የመለወጫ ጊዜ ነው። ይህ ወቅት ለመንፈሳዊ እድገት እንቅፋት የሚሆኑትን በርካታ የችግር ሰንሰለቶች የመበጠሻ ጊዜ ነው። ወቅቱ የእግዚአብሔር መለኮታዊ ሃይሉና ጥበቃው በሕይወታችን ላይ ካስቀመጣቸው ከነዚያ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ጋርም የአንድነት መተሳሰሪያ ገመዳችንን የምናጠብቅበት ጊዜ ነው፡፡ አንዱ የመጠቀሚያ ዘዴያችንም የእርቅና የፍቅር ቅዱስ ምስጥር ነው፣ ይህ ምስጢር ሃጢያታችን ይቅር እንዲባል የሚደርሰን እና እውነተኛውን ውስጣዊ መለወጥ ለማግኘት የሚያስችለን ፀጋ የያዘ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፡፡

የስብከተ ገና ወራት የመጀመሪያ ሳምንት

ጌታ በእኛ ተፈልጐ መገኘት ያለበት ነው፡፡ እርሱ እኛ ዘወትር ልንፈልገው የሚገባና እንደ ተገናኘንም ወዲያውኑ ሕይወታችንን ሊለውጠው ዘወተር ተዘጋጅቶ የሚጠብቀን ነው፡፡ እርሱን ፍለጋ እንድንሔድና ልባችንና ነፍሳችን አጥብቀው የሚሹትን አምላክ ፍለጋችንን ቀጥለን እስክናገኘው ድረስ እግዚአብሐር ይደበቅብናል፡፡  በዚህ ምድር ላይ የምናሳልፈው ሕይወታችን የማያቋርጥ ፍለጋ ያለበት፣ እግዚአብሔርን እስከምናገኘው ድረስ መሻታችንን የምንቀጥልበት፣ ካገኘነውም በኋላ ለሁል ጊዜውም  ካጠገባችን ሳይለይ እንዲኖር የምናደርግበት ጊዜ ሊሆን ይገባል፡፡ በእርግጥ ከልብ የምንወደው ከሆነ እግዚአብሔርን ማግኘት ማለት ዘወትር አጥብቀን ይዘነው መቆየት ማለት ነውና፡፡

እርሱን ፍለጋ በምንሔድበት ጊዜ፤ፍለጋህ በሙሉ ልብህና ነፍስህ ከሆነ በእርግጥም ጌታን ታገኘዋለህ።

እርሱን ለመፈለግ ታዲያ እንዴት ነው ልባችንንና ነፍሳችን የምናዘጋጀው? የርሱን ትዕዛዛት ለመጠበቅ ለራሳችን ውሳኔ ባሳለፍንበት ቀን፣ የራሳችንን ማንነትና ውስጣችንን መርምረን ንስሐ ለመግባት ቁርጥ ውሳኔ ባደረግንበት ቀን የዚያን ጊዜ ስለርሱ መረዳት እንጀምራለን፣ ልናገኘው ተስፋ አድርገን ፍለጋውን የጀመርን እለት እርሱን ለማየት እንችል ዘንድ ዓይኖቻችን ይከፈታሉ፡፡ ምክንያቱም ልበ ንፁሃን እስካልሆንን ድረስ እርሱን ለማየትና ለማግኘትም አንችልምና ነው፡፡

እርሱን ለመፈለግና ለማግኘት መንገድ ከመጀመራችን በፊት ራሳችንን በጥንቃቄ መመርመርና በልባችን አዳራሽ ውስጥ የተቀመጠው ማን እንደሆነ መርምረን ማወቅ የሚገባን ሲሆን ለርሱ ለጌታችን መቀመጫ በሆነው የልባችን አዳራሽ ውስጥ ምን በመካሔድ ላይ እንደሆነ ማየትና ማወቅ አለብን፡፡ በሌላ አነጋገር እርሱን እንግዳችንን ይዘን የምንገባበትን ክፍል ማጽዳት አለብን፡፡ ጌታን ማግኘት ማለት እርሱን መያዝና በልባችን ውስጥ እንዲቀመጥ ወደ ውስጣችን ማስገባት ማለት ነውና ጌታም ወደ እኛ ለመምጣትና ከእኛ ጋር ለመኖር ይፈልጋል፡፡

እርሱን መፈለግ የሚገባን ያህል የማንፈልገው ከሆነ ምክንያቱ በንስሐ አገባባችን ላይ የሚጐድል ነገር መኖሩና እኛም ከኃጢአታችን ቅጣት ለማዳን የተፈለገውን የሕማምና የሥቃይ መስዋዕትነት ልክ አለመገንዘባችን ነው፡፡ የኃጢአተ ይቅርታን ማግኘት አስፈላጊነት ስናውቅና ልምዱም ሲኖረን ብቻ እኛን ይቅር ለማለት ዘወትር ዝግጁ ሆኖ ወደ በምንጠብቅበት ወቅት ጌታ ከልብ ተፀፅተን ፊታችንን ወደ እርሱ ለማዞር የምንችለው ያኔ ብቻ ነው፣ ከልብ በመነጨ ፍቅር እሱን መፈለግና መከተልም የምንጀምረው፣ ምክንያቱም ብዙ ኃጢአት ይቅር የተባለለት በፋንታው ደግሞ ብዙ ይወዳልና፡፡

 “ስለዚህ ተስፋ የቆረጠውን ሁሉ በርታ አይዞህ አትፍራ እግዚአብሔር ሊታደግህ ይመጣል” ት. ኢሳያስ 35፡4

እግዚአብሔር ሁሉንም ነገሮች የሠራቸው ለራሳቸው ሲል አይደለም ነገር ግን ለታላቅ ፍጥረት ነው፡፡ ሁሉ ነገር ከተዘጋጀ በኋላ የዚህን ታላቅና ሰፊ ዓለም ንጉሥና ገዢ ሠራ ሰውን ፈጠረ፡፡ መለኮታዊ አስትንፋሱን በሰው ላይ ተነፈሰ፣ ልጁም አደረገው ከዚያም ገደብና ድንበር በሌለው በዘላለማዊ ደስታ ሰውን ተካፋይ እንዲሆንለት እጅግ ከፍተኛ ጉጉት አደረበት፡፡

ሆኖም ግን ሰው ታዛዥ ባለመሆኑ የተነሣ የእግዚአብሔርን እቅድ አበላሸ፡፡ ያም ሆኖ ግን እግዚአብሔር ጨርሶ አልተወውም፣ እራቀውም፡፡ ስለዚህ አዲስና እጅግ አስደናቂ የሆነ እቅድ አዘጋጀ በህልማችን እንኳን ጨርሶ ይሆናል ብለን ያላሰብነውን ዓይነት የሰውን ልጅ እርሱ ወዳዘጋጀለት ታላቅ ደስታ ለማምጣት ነው አዲሱን ዕቅድ የነደፈው፡፡ የሰው ልጅ ዘላለማዊ ደስታን ይጐናጸፍ ዘንድ እግዚአብሔር ያለውን ታላቅ ጉጉት ለማሳየት በመለኮታዊ፣ ጥበብ፣ ሃይልና ፍቅር እስከ መናገር ደረጃ ደረሰ፡፡ አንድያና ብቸኛውን ልጁን የምስጢረ ሥላሴ ሁለተኛውን አካል የሆነውን ልጁን እጅግ አሳፋሪና አሰቃቂ የሆነውን የመስቀል ሞት እንዲሞትና በዚህም ሳቢያ የሰው ልጅ ፈጣሪው ለርሱ ያለውን ፍቅርና የዘላለምንም ደስታ እንዲያገኝ ያለውን ጉጉት እንዲገነዘብ ሁሉም ሰብዓዊ ፈጡር ደግሞ ወደ እግዚአብሔር እንዲመለስ ያንን ተወዳጅ ልጁን የሰው ልጆች ቤተሰብ አባል አድርጐ ወደ ምድር ላከው፡፡

እርሱ መለኮታዊ ሕይወት መልሶ ሰጥቶናል፣ በድጋሚ ልጆቹ አድርጐናል፣ የርሱ የሆነችው ቤተክርስቲያን አባል አድርጐናል በርሷ አማካይነትም እንደ እግዚአብሔር ልጅነታችን ይህንን ወደ ምድር የተላከውን አዳኝ ለነፍሳችን መጠበቂያ የምንወስደው ምግብና መጠጥ አድርጐ ሰጥቶናል፡፡ በሁሉም የሕይወት መከራዎችና ፈተናዎች ውስጥ ይጠብቀናል፣ ይመራናል፡፡

 ምንጭ፡ በኢትዮጲያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የሲታዊያን ማሕበር ድረ ገጽ ላይ የስብከተ ገና ወራትን መኖርና ማክበር በሚል አርእስት ከቀረበው፣ በሜሪ ሊዊስ በተጻፈው እና በሠብለወርቅ ጳውሎስ ከተተረጎመው ገጽ ላይ በሕዳር 20/2014 ዓ.ም የተወሰደ።

29 November 2021, 15:24