አለም አቀፍ የአረጋዊያን እና የአያቶች ቀን ለመጀመሪያ ጊዜ እሁድ እለት ይከበራል አለም አቀፍ የአረጋዊያን እና የአያቶች ቀን ለመጀመሪያ ጊዜ እሁድ እለት ይከበራል  

በካናዳ የምትገኘው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የአያቶችን እና አረጋውያንን ቀን ታከብራለች

የካናዳ ጳጳሳት ጉባኤ የቤተሰብ እና ሕይወት ቋሚ ኮሚቴ በቤተክርስቲያን እና በኅብረተሰብ ውስጥ የአረጋውያንን ልዩ ቦታ አጉልቶ እንደ ሚያሳይ የገለጸ ሲሆን ይህንን የገለጸው ደግሞ በሚቀጥለው እሁድ ሐምሌ 18/2013 ዓ.ም በአለም አቀፍ ደረጃ የሚከበረውን የአረጋውያን እና የአያቶች የዓለም ቀን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ እንደ ሆነ ተገልጿል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ ቫቲካን

ለመጀመሪያ ጊዜ የሚከበረው የአያቶች እና የአረጋውያን የዓለም አቀፍ ቀን እሁድ ሐምሌ 18/2013 ዓ.ም  “ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” (ማቴ 28፡20) በሚል መሪ ቃል እንደ ሚከበር ይታወቃል። ከመክፈቻው ቀን በፊት የካናዳ ጳጳሳት ጉባሄ የቤተሰብ እና ሕይወት ቋሚ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ ወጣቶች ፣ ቤተሰቦች እና ማህበረሰቦች እንዲቀራረቡ እና ከአያቶች እና ከአዛውንቶች ጋር ጊዜ እንዲያሳልፉ ፣ አስፈላጊ ሚናቸውን ከፍ አድርገው እንዲመለከቱ የሚጋብዝ የቪዲዮ መልእክት ያፋ ማደረጉ የተገለጸ ሲሆን ቤተክርስቲያን በኅብረተሰብ ውስጥ  ከፍተኛ ሚና እንዳላት መልክእክቱ አክሎ ገልጿል።

ይህ የመጀመሪያው የዓለም የአያቶች እና የአረጋዊያን ቀን ከመጋቢት 10/2013 እስከ ሰኔ 2014 ዓ.ም ድረስ  ለሚዘልቀው በላቲን ቋንቋ “Amoris Laetitia” በአማረኛው የፍቅር ሐሴት በሚል አርዕስት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ያፋ ያደረጉት ሐዋርያው ቃለ ምዕዳን ለመዘከር እና ፍቅር በቤተሰብ ውስጥ ያለው ሚናን ለማጉላት ታስቦ የቤተሰብ ዓመት እንዲከበር ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ በወሰኑት መሰረት ከዚህ ጋር በተያያዘ መልኩ የአያቶች እና የአረጋዊያን ቀን እንዲከበር መወሰኑንም ከዚህ ቀደም መግለጻችን ይታወሳል።

የካናዳ ጳጳሳት ጉባኤ የቤተሰብ እና ሕይወት ቋሚ ኮሚቴ በቪዲዮ ያፋ ባደርገው መልእክት እንደ ገለጸው ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ አረጋዊያን “በህብረተሰቡ ውስጥ ህይወትን የሚደግፉ እና የሚመሩ የጋራ ማህበራችንን የሚጠብቁ” እንደሆኑ መግለጻቸው ያስታወሰ ሲሆን “እናንተ ጽኑ እና ጠንካራ የእምነት ጠባቂዎች ናችሁ” ማለታቸውንም አክሎ ገልጿል።

በተጨማሪም የቪዲዮ መልእክቱ እንደ ገለጸው አዛውንቶች በጣም ብዙ ጊዜ “የእኛ ታሪክ ጸሐፊዎች” ፣ የልጅ ልጆችን እና የወጣት ትውልዶችን ከጎናቸው በመሰብሰብ ቤተሰቦቻችንን ፣ ታሪካችንን ፣ ማህበረሰባችንን እና ዓለማችንን በተሻለ እንዲገነዘቡ ይረዳሉ” ማለታቸው ተገልጿል።

አያቶች ካለፈው ፣ ከአሁኑ እና ከወደፊቱ ጋር ይገናኛሉ

የካናዳ የካቶሊክ ብጹዕን ጳጳሳት ጉባኤ የሕይወት እና የቤተሰብ ቋሚ ኮሚቴ በቪዲዮ ባሰራጨው መልእክቱ አክሎ እንደ ገለጸው በተጨማሪ የአያቶች እና የአዛውንቶች ታሪኮች እና ልምዶች “ወጣቶች በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ዘላቂ እውነት ፣ ጥሩነት እና ውበት አለ ብለው እንዲያልሙ እና እንዲያከብሩ ያስችላቸዋል” ያለ ሲሆን ምክንያቱም ያለፈውን ሲያስታውሱ እና ሲያገናኙም “ የአሁኑን እና የወደፊቱን ጊዜ የሚያገናኙ ጠንካራ ምስክሮች ናቸው” ብሏል።

የካናዳ የካቶሊክ ብጹዕን ጳጳሳት ጉባኤ የሕይወት እና የቤተሰብ ቋሚ ኮሚቴ በቪዲዮ ባሰራጨው መልእክቱ አክሎ እንደ ገለጸው አረጋውያንን “እባካችሁን ጌታ በሕይወታችሁ ሁሉ ከእናንተ ጋር የተጓዘባቸውን መንገዶች በፍቅር ፣ በርህራሄ እና በጋለ ስሜት ማጋራታችሁን ቀጥሉ” ሲል አሳስቧል። የእምነት ዘሮችን እንዴት መዝራት እና መንከባከብ እንደሚችሉ በማሳየት የልጅ ልጆቻችሁን ብርህ አድርጓቸው በማለት አክሎ ገልጿል።

የወንጌል ተልእኮ ፣ አዋጅ እና ጸሎት

የቪድዮ መልእክቱ በመቀጠል ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ አረጋውያን በአደራ የተሰጣቸውን የወንጌል ስርጭት ፣ የአዋጅ እና የጸሎት ተልእኮ በማስታወስ በቤተሰቦቻቸው እና በማህበረሰቦቻቸው ላይ ፀጋን እንዲያፈሱ  እንዲፀልዩ እና የወንጌል ደስታ ህይወታቸውን እንዲለውጥ ጥሪ ማቅረባቸውን የገለጸ ሲሆን የሚሠቃዩትን እና የጠፋው አንዲመለስ ማበረታታቸውን እንዲቀጥሉ ጥሪ ማቅረባቸውን አመልክቷል።

ወጣቶች ለወደፊቱ በሕልማቸው እንዲያምኑ እንዲረዷቸው እና ምኞታችንም እናንተ የእግዚአብሔር የሕይወት ስጦታ ድንቅ እና ውበት ማሰላሰላችሁን እንድትቀጥሉ በማለት አክሎ ጥሪ አቅርቧል።

የካናዳ የካቶሊክ ብጹዕን ጳጳሳት ጉባኤ የሕይወት እና የቤተሰብ ቋሚ ኮሚቴ በቪዲዮ ባሰራጨው መልእክቱ አክሎ እንደ ገለጸው አያቶች እና አረጋዊያን በወረርሽኙ እና በሚያስከትለው ውጤት ተስፋ እንዳይቆርጡ ያሳሰቡ ሲሆን እርስ በእርስ በመደጋገፍና እርስ በእርስ በመረዳዳት “በሀዘን እና በመገለል ከሚመጣ የልብ ህመም እንፈውሳለን” በማለት ገልጿል።

የካናዳ የካቶሊክ ብጹዕን ጳጳሳት ጉባኤ የሕይወት እና የቤተሰብ ቋሚ ኮሚቴ በቪዲዮ ባሰራጨው መልእክቱ ማጠናቀቂያ ላይ ለሁሉም አያቶች እና አረጋውያን የምስጋና ማስታወሻ እና እያንዳንዳችን ደካማ ጎናችንን እና ውስንነታችንን በመያዝ በዚህ የኑሮ ደረጃ ከእነሱ ጋር አብረን እንድንሄድ ጥሪ በማቅረብ እና “የሕይወትን መንገድ ታሳየኛለህ፤ በአንተ ዘንድ የደስታ ሙላት፣ በቀኝህም የዘላለም ፍሥሓ አለ” (መዝሙር 16፡11) በሚለው ጥቅስ ነበር የቪዲዮ መልእክቱ የተጠናቀቀው።

እሁድ ጥር 23/2013 ዓ.ም የእግዚአብሔር መልአክ ማርያምን ያበሰረበትን የብስራተ ገብሬል ጸሎት ከደገሙ በኋላ ነበር ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ለአያቶች እና ለአረጋውያን መታሰቢያ የሚሆን የዓለም አቀፍ ቀን በቤተክርስቲያን ደረጃ እንዲከበር የወሰኑት። ይህም እለት በየአመቱ በሐምሌ ወር በአራተኛው ሳምንት እሁድ እለት የሚከበረውን የኢየሱስ አያቶች የሆኑት የቅዱሳን ኢያቄም እና ሃና በዓል ጋር መሳ ለመሳ እንደ ሚከበር ቅዱስነታቸው መግለጻቸው ይታወሳል።

አዛውንቶች መዘንጋት የለባቸውም

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በወቅቱ ያስተላለፉትን መልእክት ሲቀጥሉ የአያቶች እና የአረጋውያን ቀን እንዲከበር የወሰኑበትን ያወሱ ሲሆን ምክንያቱም “አያቶች ብዙውን ጊዜ ይዘነጋሉ፣ እናም አረጋውያን የተቀበሉትን ስር መሰረቶቻችንን በመጠበቅ እና በማስተላለፍ ይህን ሀብት እንዳንረሳ ለማደረግ ታቅዶ የሚከበር ቀን ነው” ማለታቸው ይታወሳል።

አያቶች እና የልጅ ልጆች እርስ በእርስ መገናኘታቸው አስፈላጊነት ላይ ቅዱስነታቸው አፅንዖት ሰጥተዋል ፣ ምክንያቱም “ነቢዩ ኢዩኤል እንደሚለው ፣ አያቶች የልጅ ልጆቻቸውን ሲያዩ ወጣቶች ደግሞ ከአያቶቻቸው ጥንካሬን በማግኘት ወደ ፊት በመሄድ ትንቢት ይናገራሉ” በማለት ስለሚመክረን ነው ብለዋል።

የአሞሪስ ላቲቲያ (የፍቅር ሐሴት) የቤተሰብ ዓመት የመጀመሪያ ፍሬዎች

የምዕመናን፣ የቤተሰብን እና የሕይወት ጉዳይ በበላይነት የሚመለከተው እና የሚቆጣጠረው የቅድስት መንበር ጳጳሳዊ ምክር ቤት ዋና ጸሐፊ የሆኑት ብጽዕ ካርዲናል ኬቪን ፋሬል ይህንን በዓለም አቀፍ ደረጃ በምትገኘው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የሚከበረው  የመጀመርያው የአያቶች እና የአረጋዊያንን ቀን ተከትሎ በወቅቱ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ የአያቶች እና የአረጋውያን ቀን መመስረት “የአሞሪስ ላቲቲያ (የፍቅር ሐሴት ሐዋርያዊ ማሳሰቢያ) የቤተሰብ አመት የመጀመሪያ ፍሬ ነው ማለታቸው የተገለጸ ሲሆን አያቶች እና አረጋዊያን ለመላው ቤተክርስቲያን ስጦታ መሆናቸው እንዲቀጥል ታስቦ የሚከበር ቀን ነው ብለዋል።

አክለውም “ከእንግዲህ በማንኛውም የክርስቲያን ማህበረሰብ ውስጥ ለአረጋውያን የሚደርገው ሐዋርያዊ እንክብካቤ ችላ የማይባል እና ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው። ‘ሁላችንም ወንድማማቾች ነን’ በሚለው ጳጳሳዊ መልእክት ውስጥ ቅዱስ አባታችን ማንም ብቻውን እንደማይድን ያስታውሰናል። ይህን በአእምሯችን ይዘን ከትውልድ ወደ ትውልድ የተላለፈውን መንፈሳዊና ሰብዓዊ ሀብት ከፍ አድርገን ልንመለከተው ይገባል ” ማለታቸው ይታወሳል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በወቅቱ የዓለም የጤና እክሎችን ከግምት ባስገባ መልኩ በመጭው ሐምሌ 18/2013 ዓ.ም እሁድ ምሽት ላይ በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ውስጥ ይህንን የመጀመሪያውን የአረጋዊያን እና የአያቶች ዓለም አቀፍ ቀን ምክንያት በማደረግ መስዋዕተ ቅዳሴ በማሳረግ እራሳቸው ራሳቸው በመምራት የመጀመሪያውን የዓለም አቀፍ ቀን ያከብራሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የምዕመናን፣ የቤተሰብን እና የሕይወት ጉዳይን የሚመለክቱ ነገሮችን በበላይነት የሚቆጣጠረው የቅድስት መንበር ጳጳሳዊ ምክር ቤት ዋና ጸሐፊ የሆኑት ብጽዕ ካርዲናል ኬቪን ፋሬል አክለው ገለጸዋል።

ለርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ቅድሚያ የሚሰጧቸው ጉዳዮች

የምዕመናን፣ የቤተሰብን እና የሕይወት ጉዳይን የሚመለክቱ ነገሮችን በበላይነት የሚቆጣጠረው የቅድስት መንበር ጳጳሳዊ ምክር ቤት ውስጥ የሚሰሩት አቶ ቪቶሪኦ ሼልዞ ለአረጋውያን በሚደረገው ሐዋርያዊ እንክብካቤ ውስጥ ተሳታፊ ናቸው። የአያቶች እና የአረጋውያን የዓለም ቀን መከበር ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ ለእግዚአብሄር ቃል እና ለድሆች ከተመሠረቱት አለም አቀፍ ቀናት ጋር የተቆራኘ መሆኑን ገልጸዋል። አቶ ቪቶሪኦ ሼልዞ ከቫቲካን ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ “ድሆች ፣ መጽሐፍ ቅዱስ እና አዛውንቶች” የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት  ፍራንቸስኮስ በጵጵስና ዘመናቸው ውስጥ “ቅድሚያ የሚሰጣቸው ጉዳዮች” እንደሆኑና “የቤተክርስቲያኗን የወደፊት ዕጣ ፈንታ ለማለም” ተብለው የተቀመጡ ጉዳዮች መሆናቸውን አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።

በአረጋውያን እና በወጣት ትውልድ መካከል ያለውን ልዩነት መቀነስ አስፈላጊ ነው ያሉት አቶ ቪቶሪኦ ሼልዞ “አዛውንቶች በራሳቸው አያድኑም። እንደ አለመታደል ሆኖ በወረርሽኙ ወቅት ስንት አዛውንቶች እንደ ተጎዱ ተመልክተናል። ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በተመሳሳይ ሁኔታ “ወጣቶች ፣ ጎልማሶች እና ህብረተሰባችን ያለ አዛውንቶች እራሳቸውን ማዳን እንደማይችሉ” ሊያስታውሱን ይፈልጋሉ በማለት ተናግረዋል። በተለያዩ ደረጃዎች ውስጥ በሚገኙ ትውልዶች መካከል ውይይት ማደረግ አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመው “ከቀውስ ውስጥ  በተሻለ እና ጥሩ በሆነ መልኩ እና ሁኔታ ለመውጣት እያንዳንዱ ህብረተሰብ ከሥር መሰረቱ ጋር መግባባት እና ከአረጋውያን ጋር ከመወያየት ጀምሮ አዳዲስ እሴቶችን ማቀናጀት ይኖርበታል” ብለዋል።

የአረጋውያን ሕልሞች

አቶ ቪቶሪኦ ሼልዞ ንግግራቸውን ሲቀጥሉ “የማግለል ባሕል ተቃራኒው ለአዛውንቶች በትክክል ሐዋርያዊ እንክብካቤ ማደረግ ነው - አዛውንቶችን በየቀኑ በአካባቢያችን የሕይወት ማእከል ውስጥ ማስቀመጥ ይኖርብናል። በድንገተኛ ሁኔታዎች ብቻ ውስጥ ሳይሆን ይህንን ለመገንዘብ ሳንዘገይ ለአረጋዊያን በተቻለን አቅም እንክብካቤ ማደረግ ይኖርብናል” ብለዋል።

አረጋውያኑ “ሁልጊዜ ፍሬ የሚሰጡ ዛፎች እና ሕልማቸውን የሚቀጥሉ ሰዎች” ናቸው በማለት የተናገሩት አቶ ቪቶሪኦ ሼልዞ ስለዚህ ወጣቶች “ከአረጋውያን ህልም ጋር ወደ ውይይት መምጣት” አለባቸው ብለዋል። ይህ ብዙውን ጊዜ በርዕሰ ሊቀ ጳጳስ ፍራንቸስኮስ የሚደጋገም መልእክት መሆኑን ጨምረው ያስታውሱት አቶ ቪቶሪኦ ሼልዞ የአረጋውያን ህልሞች ህብረተሰባችንን ገንብተዋል፣ ለምሳሌ እኔ አውሮፓን እያሰብኩ ያለሁት ከእንግዲህ ጦርነት የሌለበት ዓለም አድርጌ ነው፣ ‘ሁላችንም ወንድማማቾች ነን’ የተሰኘው ጳጳሳዊ መልእክት “ጦርነት የሌለበት ዓለም በዚህ ህልም” የተሞላ ነው፣ “አረጋዊያን እና አያቶቻችን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ” ያዩት ህልም ነው በማለት አክለው ገልጸዋል።

አቶ ቪቶሪኦ ሼልዞ አክለው እንደ ገለጹት “ምናልባት ለኅብረተሰባችን የወደፊት ህልሞች ምን መሆን እንደሚገባቸው ለመረዳት“ ከእነዚህ ህልሞች ጋር ወደ ውይይት መግባት አለብን ” በማለት ከቫቲካን ኒውስ ጋር የነበራቸውን ቆይታ አጠናቀዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ በበኩላቸው እንደ የአውሮፓዊያኑ የቀን አቆጣጠር በመስከረም 28/2018 ዓ.ም ከአረጋዊያን ጋር በተገናኙበት ወቅት በወቅቱ እንደ ገለጹት “አረጋዊያን ፍሬዎቻቸውን ይዘው እስከ መጨረሻ እንደ ሚዘልቁ ዛፎች ናቸው፣ ምንም እንኳን የእድሜ ጫና ቢኖርባቸው፣ ለአንድ ማኅበርሰብ እውነተኛ የሆነ ገጸ በረከት በመሆን እና የሕይወት ባሕል ተጠብቆ እንዲቀጥል የራሳቸውን ከፍተኛ የሆነ አሰተዋጾ ያደርጋሉ” ማለታቸው ይታወሳል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ አረጋዊያንን በተመለከተ በርከት ያሉ ንግግሮችን ማድረጋቸው የሚታወቅ ሲሆን በተለይም ደግሞ “የአረጋዊያን ጸሎት ለቤተክርስትያን በረከት ያስገኛል” በማለት በተደጋጋሚ መናገራቸው ይታወሳል። ይህንን በተመለከተ ቅዱስነታቸው ሲናገሩ የሚከተለውን ብለዋል. . .

"የአዛውንቶችና የአያቶቻችን ጸሎት ለቤተክርስትያን ጸጋ እና ሐብት ነው! ለጠቅላላው ሰብአዊ ማኅበረሰብ በተለይም ደግሞ በሥራ ለተጠመዱ፣ በብዙ ሐሳቦች ለተወሰዱ እና በጣም ለተረበሹ የማኅበርሰባችን ክፍሎች በሙሉ ከፍተኛ የጥበብ ምንጭ እና መርህ ነው! አዛውንቶችንና አያቶቻችን ማክበር፣ ለእነርሱ መጸለይ እና መዘመር ያስፈልጋል”።

23 July 2021, 14:31