የየካቲት 29/2012 ዓ.ም 1ኛው የዐብይ ጾም ሳምንት የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ የየካቲት 29/2012 ዓ.ም 1ኛው የዐብይ ጾም ሳምንት የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ 

የየካቲት 29/2012 ዓ.ም 1ኛው የዐብይ ጾም ሳምንት የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ

“ከዲያቢሎስ ጋር በፍጹም መወያየት አያስፈልግም”

የእለቱ ምንባባት

1.    ዘፍጥረት 2፡7-9፣ 3፡1-7

2.   መዝ 50

3.   ሮም 5፡12-19

4.   ማቴ. 4፡ 1-11

የእለቱ ቅዱስ ወንጌል 

የኢየሱስ መፈተን

ከዚህ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ኢየሱስን በዲያብሎስ ይፈተን ዘንድ ወደ ምድረ በዳ ወሰደው። አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከጾመ በኋላ ተራበ። ፈታኙም ወደ ኢየሱስ ቀርቦ፣ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ እነዚህን ድንጋዮች እንጀራ እንዲሆኑ እዘዝ” አለው።ኢየሱስም፣ “ ‘ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣው ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም’ ተብሎ ተጽፎአል” ሲል መለሰለት። ቀጥሎም ዲያብሎስ ኢየሱስን ወደ ቅድስት ከተማ በመውሰድ ከቤተ መቅደሱም ዐናት ላይ አውጥቶ፣ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ ራስህን ወደ መሬት ወርውር፤ እንዲህ ተብሎ ተጽፎአልና፤ “ ‘እግርህ በድንጋይ እንዳይሰናከል፣ በእጃቸው ያነሡህ ዘንድ፣ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝልሃል።’ ”

ኢየሱስም፣ “እንደዚሁም በመጻሕፍት፣ ‘እግዚአብሔር አምላክህን አትፈታተነው’ ተብሎ ተጽፎአል” በማለት መለሰለት። እንደ ገናም ዲያብሎስ ኢየሱስን እጅግ ከፍ ወዳለ ተራራ አወጣው፤ የዓለምንም መንግሥታት ከነክብራቸው አሳየውና፣ “ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ” አለው። ኢየሱስም፣ “አንተ ሰይጣን ከፊቴ ራቅ! ‘ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ እርሱንም ብቻ አምልክ’ ተብሎ ተጽፎአልና” አለው።ከዚያም ዲያብሎስ ትቶት ሄደ፤ መላእክትም መጥተው አገለገሉት።

 

የእለቱ ቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ

የተወደዳችሁ ወንድሞች እና እህቶች እንደምን አረፈዳችሁ!

በዚህ የመጀመሪያው የዐብይ ጾም እለተ ሰንበት ላይ የተነበበልን ቅዱስ ወንጌል (ማቴ. 4፡1-11) ኢየሱስ በዮርዳኖስ ወንዝ ከተጠመቀ በኋላ “መንፈስ ቅዱስ ኢየሱስን በዲያብሎስ ይፈተን ዘንድ ወደ ምድረ በዳ ወሰደው” (ማቴ 4፡1) በማለት ይናገራል። እርሱ መንግሥተ ሰማያትን የማወጅ ተልእኮውን ለመጀመር ተዘጋጅቷል፣ እናም ልክ እንደ ሙሴ እና ኤልያስ (ዘጸሐት 24 ፣ 18 ፣ 1 ነገስት 19፡8) ለአርባ ቀናት ጾመ።

በዚህ የአርባ ቀን ጾም ማብቂያ ላይ ፈታኙ ዲያቢሎስ ኢየሱስን ችግር ውስጥ ለመክተት ሦስት ጊዜ ፈተነው። የመጀመሪያ ሙከራው ኢየሱስ የተራበ መሆኑን በማሰብ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ እነዚህን ድንጋዮች እንጀራ እንዲሆኑ እዘዝ” (ማቴ 4፡3) በማለት ሐሳብ ያቀርባል። ነገር ግን የኢየሱስ መልስ ግልፅ ነበረ “ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም ተብሎ ተጽፎአል” (ማቴ 4፡ 4) በማለት ይመልሳል። እርሱም በምደረ በዳ ውስጥ በተደርገው ረጂም ጉዞ ውስጥ ሕዝቡን በመራበት ወቅት ሕይወቱ በእግዚአብሔር ቃል ላይ የተመሠረተ መሆኑን የተማረውና ሙሴን ያስታውሳል (ኦ. ዘዳግም 8፡3)።

በሁለተኛው ሙከራ (ማቴ. 4፡5-6) ዲያቢሎስ የበለጠ ብልህ ሆኗል፣ ቅዱሳት መጻሕፍትንም መጥቀስ ይጀምራል። እየተከተለ የሚገኘው ዘዴ ግልፅ ነው - በእግዚአብሔር ኃይል ላይ እጅግ በጣም የምትተማመን ከሆነ እንግዲህ ይህንን መተማመን አሳየኝ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ራስህን ወደ መሬት ወርውር፤ እንዲህ ተብሎ ተጽፎአልና” (ማቴ 4፡6) በማለት ይጠይቀዋል።   ነገር ግን በዚህ ጉዳይ ላይ እንኳን ኢየሱስ እራሱን ግራ ሊያጋባ አላሰበም፣ ምክንያቱም አንድ አማኝ የሆነ ሰው እግዚአብሔር እንደማይፈትነው ያውቃል፣ በእርሱ መልካም ፈቃድ ይተማማናል። ስለዚህ ሰይጣን እንደመሳሪያ በመጠቀም በማጣቀሻነት በመጥቀስ በተረጎመው የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ኢየሱስ ሌላ ጥቅስ ተጠቅሞ መላሽ ይሰጣል “ጌታ አምላክህን አትፈታተነውም ተብሎ ተጽፉዋል” (ማቴ 4፡7) በማለት ይመልሳል።

በመጨረሻም ሦስተኛው ሙከራ (ቁ. 8 እስከ 9) የዲያቢሎስን እውነተኛ አስተሳሰብ ያሳያል፣ የእግዚአብሔር መንግሥት መምጣት በእርሱ ላይ ድል የመቀናጃ ጅማሬ ስለሆነ ይህ ክፉ መንፈስ  የኢየሱስን ተልእኮ ከመፈፀሙ በፊ መሲሁ ፖሌቲካዊ ተልዕኮ እንዲኖረው ለማደረግ በማሰብ የእርሱን ተልዕኮ አቅጣጫ ለማስቀየር ይፈልጋል። ነገር ግን ኢየሱስ እንደ ጣዖት የሆነውን ምድራዊ ስልጣን እና ሰብዓዊ ክብር አምላኪነትን አልቀበልም በማለት በመጨረሻም ስይጣንን “አንተ ሰይጣን ከፊቴ ራቅ! ‘ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ እርሱንም ብቻ አምልክ’ ተብሎ ተጽፎአልና” (ማቴ 4፡10) አለው። እናም በዚህ ነጥብ ኢየሱስ ለእግዚኣብሔር አባቱ ያለውን ታማኝነት ከገለጸ በኋላ መላእክት እሱን ማገልገል ይጀምራሉ (ማቴ 4፡11)።

ዛሬም ቢሆን ሰይጣን የሰዎችን ሐሳቦች ለመፈተን በሰዎች ሕይወት ውስጥ ገብቷል፣ ሕሊናን ብቻ ለማርካት ከሚሞክሩ ብዙ ድምጾች ጋር ተቀላቅሉዋል። ከብዙ ማዕዘኖች የሚመጡ ለሕይወታችን ደስታን የሚሰጡ የሚመስሉ መልእክቶች እና ፈትናዎች ይመጣሉ። ራስን መቻል እንዳለብን፣ የህይወት እርካታን፣ ለራሳችን የህይወትን ደስታ የሚሰጡን ከእግዚአብሔር ይልቅ ብዙ አማራጭ መንገዶችን እንድንመለከት የሚያደርግ ሙከራ መሆኑን የኢየሱስ ተሞክሮ ያስተምረናል። ነገር ግን ይህ ሁሉ ቅዤት ነው፣ ዲያቢሎስ በሚያሳየን መንገድ የምንጓዝ ከሆነ ከእግዚኣብሔር እንርቃለን፣ ከእግዚኣብሔር እየራቅን በምንሄድበት ወቅት ደግሞ ወዲያውኑ የሚጠብቀን የሚከላከልልን ማንም እንደሌለ እንገነዘባለን፣ ታላላቅ የሆኑ ፈተናዎች እና ችግሮች በሚገጥሙን ቁጥር ለመቋቋም እንቸገራለን፣ ከእዚያም አቅመ ቢስ እንደሆንን እንረዳለን።

የእባቡን ጭንቅላት የቀጠቀጠችሁ እመቤታችን ድንግል ማርያም በዚህ በያዝነው የዐብይ ጾም ወቅት ፈትና በሚገጥመን ወቅት ጠንቃቃ እንድንሆን፣ ለዚህ ዓለም ጣዖት እንዳንገዛ፣ ከክፉ መንፈስ ጋር የሚደርገውን ውጊያ ማሽነፍ እንችል ዘንድ ኢየሱስን እንድንከተለው፣ እኛም እንደ እርሱ አሸናፊዎች ሁነን መውጣት እንችል ዘንድ እንድትረዳን አማላጅነቷን ልንማጸን ይገባል።

ምንጭ፡ ር.ሊ.ጳ ፍራንቸስኮስ በየካቲት 22/2012 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ካደረጉት አስተንትኖ የተወሰደ።

የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

07 March 2020, 14:10