ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ፒዬር ባቲስታ ፒሳባላ፣ በመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት ላይ፣                     ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ፒዬር ባቲስታ ፒሳባላ፣ በመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት ላይ፣  

የጎርጎሮሳዊያኑ አዲስ ዓመት የጋራ ውይይት የሚደረግበት ዓመት እንዲሆን ጥሪ ቀረበ።

ትናንት እሑድ ታኅሳስ 19/2012 ዓ. ም. የላቲን ሥርዓተ አምልኮን በምትከተል ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ዘንድ ተከብሮ የዋለውን የቅዱስ ቤተሰብ ቀን ምክንያት በማደረግ፣ በኢየሩሳሌም የላቲን ሥርዓተ አምልኮን የሚትከተል ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሐዋርያዊ አስተዳዳሪ የሆኑት፣ ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ፒዬር ባቲስታ ፒሳቤላ፣ በዕለቱ ባሳረጉት የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት ላይ ባሰሙት ስብከተ ወንጌል፣ የጎርጎሮሳዊያኑ አዲስ ዓመት፣ 2020 ዓ. ም. በመካከለኛው የምሥራቅ አገሮች መካከል የጋራ ውይይት የሚደረግበት፣ የአካባቢው አገሮች ሕዝቦች ለጋራ ሃላፊነት የሚቆሙ ዓመት እንዲሆን ጥሪ አቅርበዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ትናንት እሑድ ታኅሳስ 19/2012 ዓ. ም. መላዋ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የናዝሬቱን ቅዱስ ቤተሰብ በማሳታወስ ጸሎት የምታቀርብበት እለት መሆኑን ያስታወሱት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ፒሳቤላ ምእመናን ጸሎታቸውን ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ወደ ቅዱስ ዮሴፍ እና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያቀርቡበት ታላቅ ዕለት መሆኑን በስብከታቸው ወቅት አስረድተዋል። የናዝሬቱ ቅዱስ ቤተሰብ ዕለታዊ ሕይወት የሚዘከርበት ዕለት መሆኑን አስረድተው ይህ በደስታ የተሞላ የደሃ ቤተሰብ ሕይወት በፍልስጤምም መታወሱን በራማላ ከተማ በሚገኝ ቅዱስ ቤተሰብ ካቴድራል ውስጥ ለተገኙት ምዕመናን ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት ሥነ ሥርዓት ገልጸዋል።

ሊቀ ጳጳሳ ብጹዕ አቡነ ፒሳቤላ ከቫቲካን ሬዲዮ ጋር ባደረገጉት ቃለ ምልልስ እንዳስታወቁት ራማላ ከአሸባሪዎች በኩል ብዙን ጊዜ ጥቃት የሚፈጸምበት ከተማ መሆኑን ገልጸው በከተማው ውስጥ በራካታ ካቶሊካዊ ምዕመናን የሚገኙበት የቅዱስ ቤተሰብ ካቴድራል የሚገኝ መሆኑን ተናግረዋል። በዕለቱ በርካታ ምእመናን የመስዋዕተ ቅዳሴን ጸሎት መካፈላቸውን የገለጹት ሊቀ ጳጳሱ በጸሎት ሥነ ሥርዓት ለተገኙት በርካታ ቤተሰቦች ቡራኬን መስጠታቸውን እና ከምዕመናን በኩል የሚቀርቡትን ድምጾች ለማዳመጥ ዕድል ያገኙበት እና ከርካታ ሕጻናት ጋር ለመገናኘት የቻሉበት ዕለት መሆኑን ብጹዕ አቡነ ፒሳቤላ ተናግረዋል።

በፍልስጤም ውስጥ በራማላ ከተማ የሚገኝ የቅዱስ ቤተሰብ ቁምስና ከቅርብ ዓመታት ወዲያ ከፍተኛ የምዕመናን ቁጥር የጨመረበት መሆኑን ያስረዱት ብጹዕ አቡነ ፒሳቤላ ለዚህም ዋና ምክንያት ከገጠር አካባቢዎች ተሰድደው የሚመጡ በርካታ ምዕመናን በመኖራቸው ነው ብለዋል። በሌሎች አካባቢዎች እንደሚታየው ሁሉ በራማላም በርካታ ወጣቶች እና ቤተሰቦች በመኖሪያ ቤት እና በሥራ እጦት የተነሳ ዕለታዊ ሕይወታቸውን በአግባቡ ለመምራት የሚቸገሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።

ቢሆንም በብርሃነ ልደቱ ወቅት በቤተልሔም እና አካባቢዋ የደስታ ስሜት የሚታይበት መሆኑን የገለጹት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ፒሳቤላ፣ ዘንድሮ ባለተለመደ መልኩ ከተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች የሚመጡ የነጋዲያን ቁጥር ወርዶ የታየበት መሆኑን አስረድተዋል። ቢሆንም የጎርጎሮሳዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ ምዕመናን ዘንድ የተከበረውን የቅዱስ ቤተሰብ ክብረ በዓል ለመታደም ከአካባቢው በርካታ ምመናን የተገኝ መሆኑን ከጋዛ ከተማ ወደ ራማላ በመምጣት በክብረ በዓሉ ላይ ለመገኘት ጥያቄ ካቀረቡት 900 ምዕመና 300 የሚሆኑ ፈቃድ ማግኘታቸውን ገልጸው በዓሉ ደማቅ እና ሰላማዊ እንደነበርም ሊቀ ጳጳስ ፒሳቤላ አስረድተዋል።

በአካባቢው የተኩስ ልውውጥ መሰማቱ የተለመደ መሆኑን የገለጹት ሊቀ ጳጳስ ፒሳቤላ በጋዛ የጸጥታ ሁኔታ አስጊ መሆኑን ተናግረው በአካባቢው ከዕለታት አንድ ቀን ሰላም እንደሚወርድ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል። በጋዛ ውስጥ መግቢያ መውጫ ባጡት ወጣቶች መካከል ከፍተኛ የሥራ ማጣት ችግር እንዳለ ገልጸው በአካባቢው የሥራ አጥ ቁጥር ወደ 60 ከመቶ መድረሱንም ተናግረው ይህም የነዋሪውን ሕይወት አደጋ ላይ መጣሉን አስረድተዋል። ለዚህ ሁሉ ዋና ምክንያቱ በአካባቢው ሕዝቦች መካከል ቅራኔን ያዘለ ከፍተኛ ልዩነት እና ምንም ዓይነት የጋራ ውይይት አለመኖሩ ነው ብለዋል። በጋዛ ውስጥ ሕዝባዊ  ምርጫ የተካሄድው ከአሥር ዓመት በፊት መካሄዱን ያስታወሱት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ፒሳቤላ ሊገባ የተቃረበው የጎርጎሮሳዊያኑ 2020 ዓ. ም. የእምነት ተቋማትን ጨምሮ መላው የአካባቢው ሕዝብ እና የሕዝብ ተወካዮች ሃላፊነትን በመውሰድ እርስ በእርስ የሚወያዩበት እና የሚመካከሩበት ዓመት እንደሚሆን ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል።

ይህን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከዚህ ቀጥሎ የሚገኘውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
30 December 2019, 17:23