ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነኢየሱስ ሱራፌል ለመላው ካቶሊካውያን የጸሎት ቀን አወጁ፡፡
የኢትዮጵያ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ጳጳሳት ጉባዔ ፕሬዚዳንት ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነኢየሱስ ሱራፌል ለመላው ካቶሊካውያን የጸሎት ቀን አወጁ፡፡
በኢትዮጵያ ሀገራችን በዜጎች ላይ እየደረሰ ያለው ሞት ፣ አካል ጉዳት ፣ ሰቆቃ ፣ መፈናቀል አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ በሁላችንም ውስጥ ድንጋጤ የፈጠረ ጉዳይ ሆኗል፡፡ ይህ ሁኔታ ሥር የሰደደ መሆኑ ደግሞ የበለጠ እንድንፀልይ ፤ የበለጠ ለሠላምና ለእርቅ ሥራ እንድንተጋ ኃላፊነት እንድንወስድ ያስገድደናል፡፡
ስለሆነም በኢትዮጵያና በውጭ ሀገር የምትኖሩ ካቶሊካውያን ምዕመናን ይህንን የሀገራችን ህዝቦች ሰቆቃና መከራ ሠላም ማጣት ወደ መድኃኔዓለም ክርስቶስ በማቅረብ እርሱ ራሱ ለሀገራችን ሠላምን እንዲያወርድ ዕርቅን እንዲያሰፍን እንድንማጠን በትህትና እንጠይቃችኋለን፡፡
ጥቅምት 27 ቀን 2012 ዓ.ም. የመድኃኔዓለም ዓመታዊ ክብረ በዓል ስለሚከበር በዚሁ ዕለት በሁሉም የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ቁምስናዎችና ፀሎት ቤቶች ስለሀገራችን ሠላም ፣ ስለሞቱ ፣ ስለተጎዱ ፣ ስለተፈናቀሉ ወገኖቻችን በጋራ ሆነን እንፀልያለን፡፡
የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን
06 November 2019, 12:57