የደቡብ ኮርያ ካቶሊካዊ ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ የዎም፣ የደቡብ ኮርያ ካቶሊካዊ ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ የዎም፣  

የደቡብ ኮርያ ካቶሊካዊ ምዕመናን ለሰላም በመጸለይ ላይ መሆናቸው ተገለጸ።

የደቡብ ኮርያ ካቶሊካዊ ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ የዎም፣ ምዕመናኖቻቸው ለሰላም መጸለይ፣ ይቅርታን በማድረግ እና ዕርቅን ማውረድ አስፈላጊ መሆኑን አስረድተው አገራቸው አስቸጋሪ ወቅት ላይ በምትገኝበት ባሁኑ ወቅት ካቶሊካዊ ምዕመናን በያሉበት ሆነው የሰላም እናት ወደ ሆነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት እንዲያቀርቡ አሳስበዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

በደቡብ ኮርያ ዋና ከተማ ሰኡል ሀገረ ስብከ ለሁለት ቀናት የቆየ የጸሎት ስነ ስርዓት መካሄዱ ተገለጸ። የጸሎት ስነ ስርዓቱን ያዘጋጀው በ1957 ዓ. ም. የተቋቋመው የሃገሪቱ ብሔራዊ ዕርቅ አስተባባሪ ኮሚቴ መሆኑ ታውቋል። የጸሎት ስነ ስርዓቱ በየዓመቱ ሰኔ 18 ቀን እንደሚደረግ ታውቋል።

አንድነትን እና ሰላምን ማራመድ፣

በጸሎት ስነ ስርዓቱ ወደ ሦስት ሺህ የሚጠጉ ምዕመናን መካፈላቸውን ከሥፍራው የደረሰን ዜና ገልጿል። ለጸሎት ስነ ስርዓት በተዘጋጀው መርሃ ግብር  መሠረት የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት፣ የመቁጠሪያ ጸሎት የተከናወነ ሲሆን በተጨማሪም በደቡብ ኮርያ የምትገኝ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያንን በማስመልከት ለምዕመናኑ አጭር ታሪካዊ ገለጻ ተደርጎላቸዋል። በስነ ስርዓቱ  ላይ ከሁለቱም ኮርያዎች የመጡ ብጹዓን ጳጳሳት፣ ሐዋርያዊ አስተዳደር እና የሃገረ ስብከቱ ካህናት ተካፋይ ሆነዋል።

የጸሎት እና የይቅርታ አስፈላጊነት፣

የሰኡል ከተማ ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ እንድርያስ የዎም በመስዋዕተ ቅዳሴው ስነ ስርዓት ወቅት ባቀረቡት ስብከተ ወንጌል እንዳስገነዘቡት በሁለቱ ኮርያዎች መካከል ሰላንም ለማውረድ ከተፈለገ ሳያቋርጡ መጸለይ እና ይቅርታን ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል። ከባድ የጦር መሣሪያ ውድመትን ተግባራዊ ለማድረግ ስምምነት ከተደረገ ወዲህ ምንም የረባ ለውቅጥ አልታየም ያሉት ሊቀ ጳጳሳት እንድርያስ ዘላቂ እና አስተማማኝ ሰላምን ለማምጣት መጸለይ አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል።

ጸሎት የማድረግ እቅድ፣

የሰኡል ከተማ ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ እንድርያስ የዎም፣ ከ2007 ዓ. ም. ጀምሮ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ወደ ደቡብ ኮርያ ሐዋርያዊ ጉብኝቸውን ባደረጉበት ወቅት ባቀረቡት ሃሳብ መሠረት በሰሜን ኮርያ የሚገኙት 52 ቁምስናዎችን በጸሎት ማስታወስ እንደሚገባ ማሳሰባቸውን ገልጸው በሰሜን ኮርያ በስቃይ ላይ ለሚገኙት ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ፍትህን እንዲያገኙ፣ የእምነት ነጻነት እንዲከበርላቸው በጸሎታችን እናግዛቸዋለን ብለዋል።

በሁለቱ አገሮች ሕዝቦች የመንፈስ አንድነት እንዲኖር ያስፈላጋል።

ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ እንድርያስ የዎም በማከልም በአገራቸው የስደት ሕይወትን ለሚኖሩ፣ መከራ እና ግፍ ለሚደርስባቸው የሰሜን ኮርያ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን እግዚአብሔር እገዛውን እንዲያበዛላቸው እንጸልያለን ብለዋል።

ተስፋ መቁረጥ የለብንም፣

ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ እንድርያስ የዎም አክለውም በሰሜን ኮርያ ላይ የተጣለው ከባድ የጦር መሣሪያ ምርት ማስቆም እና ማውደም በተግባር ባይታይም፣ በበኩላችን በሰሜን ኮርያ እውነተኛ ሰላም እስኪሰፍን ለዚያ ሕዝብ ወንጌልን መመስከር አናቋርጥም፣ ተስፋንም አንቆርጥም ብለዋል።

ሰሜን ኮሪያን ከኒዩክሌር የጦር መሣሪያ ነጻ ማድረግ፣

ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ እንድርያስ የዎም በማከልም እውነተኛ ሰላም የሚመጣው ይቅርታን በማድረግ ነው ብለው፣ ይቅርታ ማድረግ ቀላል ባይሆንም እግዚአብሔር በሚሰጠን ጸጋ በመታገዝ የበደሉንን ይቅር ማለት ያስፈልጋል ብለዋል።

ሁለቱም ኮርያዎች ወደ እድገት ጎዳና፣

በመጨረሻም የሰኡል ከተማ ሊቀ ጳጳሳት ብጹዕ አቡነ እንድርያስ የዎም በዚህ አስቸጋሪ ወቅት የሰላም ንግሥት የሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንድታስገኝልን፣ ሁለቱም ኮርያዎች ወደ እውነተኛ የእድገት ጎዳና እንዲገቡ ጸሎታችንን እናቀርብላታለን ብለዋል።

ይህን ዘገባ በድምጽ ለማዳመጥ ከዚህ ቀጥሎ የሚገኘውን “ተጫወት” የሚለውን ምልክት ይጫኑ!
03 July 2019, 15:04