የኢትዮጲያ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በአውሮፕላን አደጋ ሕይወታቸውን ላጡ መስዋዕተ ቅዳሴ ተደረገ የኢትዮጲያ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በአውሮፕላን አደጋ ሕይወታቸውን ላጡ መስዋዕተ ቅዳሴ ተደረገ 

ሕይወታቸውን በአይሮፕላን አደጋ ላጡ ወገኖች ሥርዓተ ፍታት ተደረገ

መጋቢት 01/2011 ዓ. ም. መላውን ዓለም በጥልቅ ያሳዘነና ያነጋገረ አሳዛኝ የአይሮፕላን አደጋ በኢትዮጲያ ተከስቶ እንደ ነበረ ይታወሳል። አደጋው እጅግ ከባድ ከመሆኑ የተነሳ በአገራችን እና በዓለም ሕዝቦች ላይ ሳይቀር ያሳደረው ተጽዕኖ እና ሐዘን ዛሬም ቢሆን አልበረደም።

የዚህ ዘገባ አዘጋጅ እና አቅራቢ ማክዳ ዮሐንስ-ኢትዮጲያ

ይህ አሳዛኝ ክስተት ዋና ጉዳቱ በተለይ ለሟች ቤተሰቦች ቢሆንም ጉዳቱን መላው ዓለም የራሱ አድርጐ ሐዘኑን ተጋርቶታል። በዚህ የተነሳ መጋቢት 5 ቀን 2011 ዓ. ም. በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኘው የመድኃኒዓለም የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ቁምስና ውስጥ በአደጋው ሕይወታቸውን ያጡ ሰዎችን በማስታወስ በመስዋዕተ ቅዳሴ ተደርጎ ሥርዓተ ፍትሃት መፈጸሙ ታውቁዋል።

መስዋዕተ ቅዳሴው እንዲደረግ በጋራ ያመቻቹት ደግሞ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን እና በኢትዮጵያ የሚኖሩ ዓለም አቀፍ የካቶሊካውያን ህብረት ማኅበር አባላት መሆናቸው የተገለጸ ሲሆኑ በመንበረ ታቦት ፊት በቀረቡት 157 ነጭ የጽጌረዳ አበባዎችን፣ 157 ሻማዎች በማብራት እና እንዲሁም የተለያዩ ዓይነት የአበባ ጉንጉኖችን በማስቀመጥ በሞት የተለዩ ወገኞች ሀገር ዜጎችን በመጥቀስ እንዲታሰቡ ተደርጉዋል።

መስዋዕተ ቅዳሴውን በበላይነት የመሩት ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነየሱስ ሊቀ ጳጳሳት ዘካቶሊካውያን ሲሆኑ ከእርሳቸው ጋር በኢትዮጰያ የቅድስት መንበር ተወካይ የሆኑት ብፁዕ ሊቀ ጳጳስ ሉዊጂ ቢያንኮ እና ከተለያዩ አገረ ስብከቶች የተውጣጡ ብጹዕን ጳጳሳት ጋር በጋራ በመሆን  መርተዋል።  በመስዋዕተ ቅዳሴው ላይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስተዳደር ተወካይ፣  የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ጠቅላይ ጸሐፊ፣ የተለያዩ አገራት ልዑካን እና አንምባሳደሮች፣ የሟች  ቤተሰብና  ወዳጆች፣ የዓለም ዓቀፍ ተቋማት ተወካዮች  ተገኝተዋል።

ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነየሱስ በወቅቱ ባደረጉት ንግግር በአደጋው እኛ ኢትዮጵያውያን ብቻ ሳንሆን የተጎዳነው መላው ዓለምን ጭምር ያሳዘነ አደጋ መሆኑን ገልጸው በአደጋው ሕይወታቸውን ላጡ ሁሉ እግዚብሔር ነፍሳቸውን በገነት እንዲያኖርልን፣ በቤተሰባቻቸው እና በወዳጆቻቸው ሞት ከባድ ሀዘን ለደረሰባቸው ወገኖች ሁሉ መጽናናትን ተመኝተዋል።

በዚሁ ሥርዓተ ፍታት ላይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስተዳዳር ተወካይ አቶ ፍቅሬ ደግፍ፣ በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግሥታት ሃላፊ ው ቬራ ሶንጌ፣ በኢትዮጵያ የኬኒያ አምባሳደር ክብርት ካትሪን ምዋንጊ ንግግር ያደጉ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ የቅድስት መንበር ተወካይ ደግሞ ር.ዕ.ሊ. ጳጳሳት ፍራንቼስኮስ ይህንን አደጋ በተመለከረ ያስተላለፉትን የሐዘን መግለጫ መልእክት አሰተላልፈዋል።

Photogallery

የኢትዮጲያ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በአውሮፕላን አደጋ ሕይወታቸውን ላጡ መስዋዕተ ቅዳሴ ተደረገ
15 March 2019, 11:37