የቀድሞው የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፕሬዚደንት ክቡር ግርማ ወልደጊዮርጊስ ከካቶሊክ ብጹዕን ጳጳሳት ጋር የቀድሞው የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፕሬዚደንት ክቡር ግርማ ወልደጊዮርጊስ ከካቶሊክ ብጹዕን ጳጳሳት ጋር 

ከኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የተሰጠ የሐዘን መግለጫ

ከወጣትነት እድሜአቸው ጀምሮ በታማኝነትና በትጋት ለአገራቸው እድገት ሲሰሩ የነበሩት የቀድሞው የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፕሬዚደንት ክቡር ግርማ ወልደጊዮርጊስ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ስንሰማ እጅግ አዝነናል፡፡ እርሳቸው አገራቸው ወደ እድገት ጎዳና እንድታመራ በተሰማሩበት ዘርፍ ሁሉ ዘመናዊ የስራ አተገባበርን በማበረታታት እንዲሁም የዘመናችን አንገብጋቢ ጉዳይ የሆነውን የአየር ንብረት ጥበቃን የህይወታቸው ጥሪ በማድረግ ሲተጉ ቆይተዋል፡፡ በዚህ ብቻ ሳይታቀቡ ነፍስሔር ግርማ ወልደጊዮርጊስ ዘመናቸውን በሙሉ የሰላም መሳሪያ በመሆን እንደ የስራ ሃላፊ፣ ርዕሰ ብሔርና አባት በመሆን አገራቸውንና ህዝባቸውን አገልግለዋል፡፡ በቀጣይም አገር ተረካቢ የሆነውም ተተኪ ትውልድ ሰላማዊና ያልተበከለ አየር የሚተነፍስባት አገር እንዲረከብ የበኩላቸውን አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡
እኛም ነፍስኄር ግርማ ወልደጊዮርጊስ በዚህች ምድር ላይ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ጸጋ ተጠቅመው ሙሉእ የሆነ ኑሮ በመኖር ስላሳለፉት ሕይወት ሁሉን ቻይ የሆነውን እግዚአብሔርን እናመሰግናል፡፡ የእርሳቸውን ነፍስ እግዚአብሔር በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያምና በቅዱሳን ሁሉ መካከል ለዘለዓለም በሰላም እንዲያሳርፍልን እንማጠናለን፡፡ ለመላው ቤተሰባቸውና ለኢትዮጵያ ህዝብም መፅናናትን እንመኛለን፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን ይባርክ!

አባ ሐጎስ ሐይሽ
ጠቅላይ ጸሐፊ
 

17 December 2018, 16:29