የሕዳር 23/2011 ዓ.ም የ33ኛ እለተ ሰንበት ቅዱስ ወንጌል እና የቅ. አስተንትኖ የሕዳር 23/2011 ዓ.ም የ33ኛ እለተ ሰንበት ቅዱስ ወንጌል እና የቅ. አስተንትኖ 

የሕዳር 23/2011 ዓ.ም የ33ኛ እለተ ሰንበት ቅዱስ ወንጌል እና የቅ. አስተንትኖ

“የተሰጡንን ጸጋዎች ለመጠቀም ከኢየሱስ ጋር መገናኘት ይኖርብናል”

በእለቱ የተነበቡት ምንባባት

1.     ት.ዳንኤል 12፡1-3

2.    መዝ. 15

3.    ዕብ. 10፡11-14

4.    ማር. 13፡24-32

 

የእለቱ ቅ. ወንጌል

የማርቆስ ወንጌል 13፡24-32

በዚያን ወራት ግን ከዚያ መከራ በኋላ ፀሐይ ይጨልማል ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም፥  ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፥ የሰማያትም ኃይላት ይናወጣሉ። በዚያን ጊዜም የሰው ልጅ በብዙ ኃይልና ክብር በደመና ሲመጣ ያዩታል።  በዚያን ጊዜም መላእክትን ይልካል ከአራቱ ነፋሳትም ከምድር ዳርቻ እስከ ሰማይ ዳርቻ የተመረጡትን ይሰበስባቸዋል።  ምሳሌውንም ከበለስ ተማሩ፤ ጫፍዋ ሲለሰልስ ቅጠልዋም ሲያቈጠቍጥ፥ ያን ጊዜ በጋ እንደ ቀረበ ታውቃላችሁ፤  እንዲሁ ደግሞ እናንተ ይህን ሁሉ መሆኑን ስታዩ ቀርቦ በደጅ እንደ ሆነ እወቁ። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም። ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም።  ስለዚያች ቀን ወይም ስለዚያች ሰዓት ግን የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ ልጅም ቢሆን ከአባት በቀር የሚያውቅ የለም።

 

የእለቱ ቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ በርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ

“የተሰጡንን ጸጋዎች ለመጠቀም ከኢየሱስ ጋር መገናኘት ይኖርብናል”

የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደ ምን አረፈዳችሁ!

በዛሬው እለተ ሰንበት በተነበበልን ቅዱስ ወንጌል (ማር.13፡24-32) ጌታ ወደ ፊት ሰለሚከሰቱ ነገሮች ለደቀ-መዛሙርቱ መግለጫ ሲሰጥ እናያለን። እሱ በዋነኝነት የሚናገረው ሰለ ዓለም መጨረሻ ሳይሆን ነገር ግን አሁን ያለውን ሕይወታችንን በጥሩ ሁኔታ ለመኖር፣ ንቁ እና ሁልጊዜ ህይወታችን በከፍተኛ ጥንቃቄ በመመልከት እንድንኖር ያቀረበልን ጥሪ ነው። በዚያን ወራት ግን ከዚያ መከራ በኋላ ፀሐይ ይጨልማል ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም፥  ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፥ የሰማያትም ኃይላት ይናወጣሉ” (ማር. 13፡24-25) በማለት ኢየሱስ ይናገራል።

እነዚህ ቃላት በዘፍጥረት መጽሐፍ የመጀመሪያ ገጽ ላይ ስለተጠቀሱት ከጥንት ጊዜ ጀምሮ ስርዓቱን በጠበቀ መልኩ ብርሃን የሚሰጡ እና የሕይወት ምልክት የሆኑትን ማለትም ሰለፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት በመግለጽ የእነሩሱ አለመኖር ደግሞ ጨለማ እና ሁከት የፍጻሜ ምልክት የሆኑት ምልክቶች እንደ ሚከሰቱ ያሳያል። በምትኩም በዚያው በመጨረሻ ቀን የሚበራ ብርሃን ልዩና አዲስ ይሆናል፣ ጌታችን ኢየሱስ ከቅዱሳን ሁሉ ጋር በክብር ይገለጻል። በዚያ የመጨረሻ ወቅት የእርሱን የሚያበራ ፊት በቅድስት ስላሴ ሙሉ በሆነ ብርሃን እንመለከታለን፣ በአጠቃላይ ለሰው ዘር በሙሉ የሚገለጥ እውነት የሆነ የፍቅር ፊት ነው። የሰው ዘር ታሪክ እንደ እያንዳንዳችን የግል ታሪክ ማለት ነው በቀላሉ በሚገለጹ ቃላት እና ተግባሮች ብቻ በመግለጽ ትርጉም ለመስጠት ያዳግታል። በዛሬው ቅዱስ ወንጌል ውስጥ ኢየሱስ የሕዝብ እና የእያንዳንዱ ሰው ታሪክ መጨረሻ እና አንድ ግብ እንዳለቸው ይናገራል፣ ይህም በመጨረሻ ከኢየሱስ ጋር መገናኘት አይቀረ መሆኑን ያሳየናል። እርሱ የሚመጣበትን ቀን እና እንዴት እንደ ሚመጣ በፍጹም ማወቅ አንችልም፣ ይህንን በተመለከተ ኢየሱስ ሲናገር ስለዚያች ቀን ወይም ስለዚያች ሰዓት ግን የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ ልጅም ቢሆን ከአባት በቀር የሚያውቅ የለም” (ማር. 13፡32) በማለት ሁሉም ነገር በእግዚኣብሔር በምስጢር እንደ ተያዘ ይናገራል። ኢየሱስ “ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም” እንዳለው እኛ ግን አንዱ ሌላውን ፊት ለፊት የምጋፈጥበት መሰረታዊ መርህ ምን እንደ ሆነ እናውቃለን። ዋነኛው ወሳኝ ነጥብ ይህ ነው። በዚያች ቀን እያንዳንዳችን የእግዚአብሔርን ልጅ የገለፀውን እና የእርሱን ሕልውና ምንጭ የሆነው ቃል የሕይወታችን ሕልውና ሆኖ እንደ ነበረ ወይም ደግሞ ለእርሱ ቃል ጀርባችንን ሰጥተን በራሳችን ቃል ላይ ብቻ ተማምነን መኖር አለመኖራችንን  እንድንመለከት ይረዳናል። ከምንጊዜ በላይ ደግሞ እስከ መጨረሻ ድረስ ለአብ ፍቅር እና ለእርሱ ምሕረት ራሳችንን  ተገዢ የምናደርገበት ወቅት ነው።

ማንም ሰው ከዚህ ቅጽበት ማምለጥ አይችልም! እኛ ታማኞች ሆነን ለመታየት በማሰብ በባህሪያችን ውስጥ የምናስገባው ብልሃት በዚያን ጊዜ ተቀባይነት የለውም፣ በተመሳሳይ መልኩ እኛ አሁን የምንመካበት የገንዘብ ኃይል ወይም ማነኛውምን ነገር ለመግዛት የሚያስችለን የኢኮኖሚ አቅም በዚያን ጊዜ ለመጠቀም አንችልም። ይዘነው ልንቀርብ የምንችለው ነገር ቢኖር በሕይወታችን ዘመን የማያለፈውን የእርሱን ቃል በሕይወታችን ተግብረን በዚህ ምክንያት ይዘነው የምንቀርበው መልካም ሥራችን ብቻ ነው፣ ከዚህ ውጪ ያሉ ሁሉም ነገሮች የከንቱ ከንቱ ናቸው። ይዘነው ልንቀርብ የምንችለው ጉዳይ ቢኖር በሕይወታችን ዘመን በነጻ የተቀበልነውን በነጻ የሰጠናቸውን መልካም ተግባሮች ብቻ ነው።

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዚህ ምድር ላይ በምንኖርበት በአሁኑ ወቅት ውስንነታችን በመገንዘብ በዚህ ምድር ላይ በፍራሃት እና በመንቀጠቀጥ ሳይሆን ነገር ግን ሕይወታችንን ኃላፊነት በተሞላው መልኩ በመኖር ለባልንጀሮቻችን የተቻለንን በማድረግ በአጠቃላይ ለዓለም በሙሉ መልካም ነገሮችን በማድረግ ሕይወታችንን በዚሁ አግባብ ብቻ ለመኖር እንችል ዘንድ እንድትረዳን አማላጅነቷን መማጸን ያስፈልጋል።

 

ምንጭ፡ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮስ እ.አ.አ በሕዳር 02/2018 ዓ.ም በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን ካሰሙት ስብከተ ወንጌል የተወሰደ

 

01 December 2018, 10:42