የፍልሰታ ማርያም በዓል የክርስቲያኖች የተስፋ ምልክት ነው። የፍልሰታ ማርያም በዓል የክርስቲያኖች የተስፋ ምልክት ነው። 

የፍልሰታ ማርያም በዓል የክርስቲያኖች የተስፋ ምልክት ነው!

የአውሮፓዊያኑን የቀን አቆጣጠር በሚከተሉ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ በነሐሴ 09/2010 ዓ.ም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ እና በነፍስ ወደ ሰማይ ያረገችበት የፍልሰታ በዓል ተከብሮ ማለፉ ይታወሳል። ይህንን ታላቅ በዓል በምናከብርበት ወቅት ምልከታችንን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም በምትገኝበት በሰማያዊው ቤታችን ላይ በማድረግ በዚያ ልጇ በምገኝበት ሰማያዊ ክብር ላይ አስተንትኖ እንድናደርግ የዛሬው ቀን ስርዓተ አምልኮ ይጋብዘናል።

የዚህ አስተንትኖ አዘጋጅ እና አቅራቢ መብራቱ ኃይሌጊዮርጊስ-ቫቲካን

የፍልሰታ በዓል ከመጀመሪያው ዘመን አንስቶ መላው የክርስቲያን ማኅበረሰብ የምያከብረው ታላቅ የሆነ በዓል ሲሆን እግዚኣብሔር አምላክችን የልጁ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ማደሪያ እንድትሆን የመረጣትን፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሚገባ በማስዳግ በእግዚኣብሔር የደኅንነት እቅድ ውስጥ ተሳታፊ የሆነችዋን፣ ታማኝ ሐዋሪያ በመሆን እስከ መጨረሻው እስከ መስቀል ሥር ድረስ የልጇን ስቃይ በትዕግስት የተመለከተችውን፣ ልጇ በመስቀል ላይ ሳለ ለተወዳጁ ሐዋሪያው ዮሐንስ “ይህችውልህ እናትህ” በማለት በአደራ በማስረከብ ከእዚያም በመቀጠል ለእኛም በምስጢረ ጥምቀት አማካይነት የክርስቶስ ሐዋሪያ ለሆንን ለእኛም እናት እንድትሆነን የተሰጠችንን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማሪያምን ክብር የምናሰላስልበት ቀን ነው የፍልሰታ በዓል።

የፍልሰታ ማርያም በዓል ጽንሰ ሐሳብ እያንዳንዳችንን የሚነካን ምስጢር በውስጣችን የሚያነሳሳ በዓል ሲሆን ይህም የምሆንበት ምክንያት በሁለተኛው የቫቲካን ጉባሄ ሰንድ ላይ እንደ ተጠቀሰው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም “እርግጠኛ የተስፋ ብርሃን ምልክት ሆና በማብራት እና የመጽናኛ ምልክት በመሆን በጉዞ ላይ የምገኙ የእግዚኣብሔር ሕዝቦችን ትመራለች” (Lumen Gentium ቁ. 68) እንደ ሚለው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም የክርስቲያኖች እናት በመሆን በችግሮቻቸው እና በተግዳሮቶቻቸው አጋዥ ሆና በመቀረብ ከልጇ ታማልዳለች፣ ጸጋም ታስገኛለች።

ነገር ግን እኛ ክርስቲያኖች በእየዕለቱ በሚያጋጥሙን ክስተቶች እና የሕይወት ተግዳሮቶች ምክንያት የተነሳ ይህንን እጅግ የሚያጽናና መንፈሳዊ እውነታ ብዙን ጊዜ እንዘነጋለን። ስለዚህ የተስፋ ብርሃን ምልክት በእኛ ማኅበረሰብ ውስጥ እየተስፋፋ እንደመጣ እርግጠኛ መሆን የምንችለው እንዴት ነው? ፈጽሞ የማይሞቱ መስሎ የምሰማቸው ብዙ ሰዎች  ዛሬ አሉ ወይም ደግሞ ሞት የክርስቲያን ሕይወት መጨረሻ እንደ ሆነ የምያስቡ ሰዎች አሉ፣ አንዳንዶች የሰው ልጅ የእራሱ የሕይወት  ብቸኛው መሐንዲስ አድርገው በመቁጠር የሰው ልጅ የራሱን የመጨረሻ ግብ እጣ እድል የሚወስነው ራሱ ግለሰቡ ነው በማለት በዚህ ዓይነት ባሕሪ ተሞልተው የምኖሩ ሰዎች አሉ፣ እግዚኣብሔር በፍጹም እንደ ሌለ አድርገው በመቁጠር፣ እንዲያውም አንዳንዴ እግዚኣብሔር በዚህ በምንኖርበት ምድራችን ላይ ምንም ዓይነት ሥፍራ እንደሌለው በመቁጠር እንዳሻቸው የምኖሩ ሰዎች አሉ። አሁን በዓለማችን የምናያቸው ምርጥ የሚባሉ የቴክኖሎጂ ስኬቶች፣ የሳይንስ ምጥቀት በማኅበራዊ ሳይንሥ ዙሪያ የምስታዋሉ ከፍተኛ ጥናቶች፣ የሰው ልጅ በተለያዩ የእውቀት ዘርፎች እየመጠቀ በመሄዱ የተነሳ የሰው ልጅ የሕይወት ሁኔታ ከቀን ወደ ቀን እየተሻሻለ መሄዱ እሙን ቢሆንም ቅሉ ነገር ግን የሰው ልጆች ከጥንት ጊዜ ጀምሮ ለነበራቸው ጥልቅ የሆነ የሕይወት ጥያቄ ግን በቂ የሆነ መልስ ሊሰጡ አልቻሉም።

የሰው ልጅ መሰረታዊ ለሆኑ የሕይወት ጥያቄዎቹ መልስ ሊያገኝ የምችለው በእዚህ ዓለም በተለያየ መልክ ከምያገኘው ጥበብ ሳይሆን ነገር ግን ጥልቅ የሆነውን የእግዚኣብሔርን የፍቅር ምስጢር በመረዳት በሕይወቱ ውስጥ ዘወትር የሚገኘውን የሕይወት፣ የፍቅር፣ የእውነት፣ የፍትሕ እና የእርካት ጥም መቁረጥ የምችለው እና ልባዊ የሆነ ደስታን መጎናጸፍ የምያስችለው ግን በእግዚኣብሔር ድጋፍ ብቻ እንደ ሆነ ግልጽ እና እሙን የሆነ ጉዳይ ነው። ለሰው ልጂ ዘለዓለማዊ ጥያቄ ዘለዓለማዊ ምላሽ የሚሰጠው እግዚኣብሔር ብቻ ነው፣ በተለይም የሰው ልጅ የሕይወት ምስጢር ሆነው ለዘለቁት ድክመቶች፣ ስቃዮች እና ሞት ለመሳሰሉ ጉዳዮች ዘላቂ ምላሽ የምናገኘው ከእግዚኣብሔር ብቻ ነው።

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሰማያዊ ክብር በምንሳታውሰበት እና በምናሰላስልበት በአሁኑ በፍልሰታ በዓል ወቅት ለእኛም ቢሆን ይህ የምንኖርበት ምድራችን የዘለዓለም ቦታችን እንዳልሆን በመረዳት፣ ይህንን ምድራዊ ሕይወታችን እግዚኣብሔር በምፈልገው መንገድ አሳምረን የምንኖር ከሆነ፣ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን በማገልገል በምንኖርበት ወቅት፣ በእግዚኣብሔር ትዕዛዝ በመመራት ሕይወታችንን በምንኖርበት ወቅት እኛንም ሰማያዊ የሆነ ክብር እንደ ምጠብቀን የምንረዳበት እና የምንገነዘብበት በዓል ነው የፍልሰታ ማሪያም በዓል። ለዚህም  ነው እንግዲህ ምንም እንኳን ብዙ ዕለታዊ ችግሮች ቢኖሩብንም ሰላምና መረጋጋት የሚሰማን በዚሁ ምክንያት ነው። እናታችን ለእኛ ዘወትር ታማልዳለች።

ታዲያ የፍለሰታ ማርያም በዓል በምናከብርበት ወቅት ራሳችንን አንድ ጥያቄ ልንጠይቅ የገባል፣ ማርያም በሰማይ ቤት ሆና ምን እየሠራች ነው? ብለን ጥይቄ ማንሳት ተገቢ ነው። ምላሹ አንድ እና አንድ ብቻ ነው፣ ማርያም በሰማይ በሰማያዊ ክብር ውስጥ ሆና የእኛ እናት መሆኑዋ ቀጥሉዋል። የእናት ተግባር ደግሞ አንድ እና አንድ ብቻ ነው፣ ይህም ለልጆቿ ሁልጊዜ ማሰብ የእናት ተቀዳሚ እና ዋነኛው ባህሪ ነው። በዚህም ምክንያት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ለእኛ ለልጆቿ ታስባለች ማለት ነው፣ በልቧ ውስጥ ባለው የእግዚኣብሔር የፍቅር እሳት አማካይነት  ለእኛ ለእያንዳንዳችን ርኅራኄን ታሳያለች፣ እንዴት እንደ ምትወደንም ታሳየናለች። ይህ የፍልሰታ ማርያም በዓል ለእኛ ለክርስቲያኖች ከፍተኝ የሆነ መጽናኛ የምሰጠን በዓል ነው፣ እኛም እምነታችንን በአግባቡ ከኖርን፣ በእግዚኣብሔር መንገድ ለመመላለስ ከሞከርን፣ እግዚኣብሔር እርስ በእርሳችሁ ተዋደዱ እንዳለን እርስ በርሳችን ከተዋደድን እኛም የሰማይ ቤት ወራሾች እንደ ሆንን የምያሳይ የተስፋ ምልክት ያዘል በዓል ነው የፍልሰታ ማርያም በዓል።

በዚህም መልኩ ብቻ ነው ምድራዊ የሆኑ ስቃዮቻችንን፣ ፈተናዎቻችንን፣ ጭንቀቶቻችንን ወደ ሰላም እና ወደ ፍቅር መቀየር የምችለው የክርስቲያኖች እናት በሆነቺ በእመቤታችን እጅግ ቅድስት ድንግል ማሪያም አማላጅነት እና ከልጇ በምታሰጠን መልኮታዊ ጸጋ ታግዘን ብቻ ነው። የሰላም እናት የሆነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በልባችን፣ በቤተሰባችን፣ በሀገራችን እንዲሁም በመላው ዓለም ሰላም እና ጤና ይስፍን ዘንድ በአማላጅነቷ ትርዳን አሜን።

15 August 2018, 09:30